tg-me.com/yemetshaf_qdus_tinat/5
Last Update:
📖መጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መግቢያ📖
✞ክፍል ሶስት✞
✨መጽሐፍ ቅዱስ በቁጥርና በምዕራፍ ማንና ለምን ከፈለው?
መጽሐፍ ቅዱስ በምዕራፍ መከፋፈሉ ከመጻሕፍቶቹ አንዱ ክፍል የያዘውን ሐሳብ በደምብ ለማጥናትና የት እንደሚገኝ ለማስታወስ ጥቅሙ ስለተረዳ የእንግሊዝ ካንተር በሪ ካርዲናል(ሊቀ ጳጳስ) ስቴቨን ላንግተን በ13ኛው ክ.ዘ. የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን በምዕራፍ ከፋፈለው።ሶስት መቶ ዓመታት አለፍ ብሎም በ1551ዓ.ም ሮበርት ስቴፋነስ የተባለ ፈረንሳዊ በምዕራፍ ያሉትን ሙሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በቁጥር ከፋፈላቸው ይህም በምዕራፍ ውስጥ ያሉትን ሐይለ ቃላት ቶሎ ለማግኘት በጣም አጋዥ ሆነ።የእነዚህ ሁለት ሰዎች ስራ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለቤተ ክርስቲያን ትልቅ ውለታ ነው።ውለታቸውም በስነ መለኮት ትምህርት(theology)፣በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ከመጽሐፍ ቅዱስ እያጣቀሱ በሚጻፉ መጻህፍት እንዲሁም በሰባክያን ዘንድ የጀርባ አጥንት በመሆን በቤተ ክርስቲያን አሰራር ላይ የማይረሳና የማይቀየር የሚመሰገንም አሻራ ሆኗል። እግዚአብሔር የድካማቸውን ዋጋ ይስጣቸው።
✨መጽሐፍ ቅዱስ የሰዎች ፈጠራ አለመሆኑና እውነተኛነቱ በምን ይታወቃል? ተብሎ ለቀረበው ጥያቄ፡-
☞በመጻሕፍቱ አንድነት ይታወቃል ይህም በተለያዩ ፀሐፊዎችና በተለያዩ ጊዜያት ውስጥ ቢፃፍም አንድ ሐሳብ አንድ ዓይነት ስሜት አላቸው።በዚህም አንዱ የእግዚአብሔር መንፈስ እንዳፃፋቸው እናውቃለን።
ስለ ነቢያቱ መጻሕፍት "21፤ ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ።"
(2ኛ የጴጥሮስ መልእክት 1:21፤)
በሐዋርያት ላይ መንፈስ ቅዱስ እንደሚሞላና እንደሚመራቸው እንጂ ከራሳቸው ፈጥረው እንደማይናገሩ
(የዮሐንስ ወንጌል 16)
----------
"13፤ ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤ የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤ የሚመጣውንም ይነግራችኋል።
14፤ እርሱ ያከብረኛል፥ ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋልና።
15፤ ለአብ ያለው ሁሉ የእኔ ነው፤ ስለዚህ። ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋል አልሁ። "
ደግሞም
(የዮሐንስ ወንጌል 15)
----------
"26፤ ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል፤
27፤ እናንተም ደግሞ ከመጀመሪያ ከእኔ ጋር ኖራችኋልና ትመሰክራላችሁ።"
✅ከዚህ እንደምንረዳው ነቢያቱን የመራውና የተናገረው የእግዚአብሔር መንፈስ፤ሐዋርያቱንም የመራና የተናገረው ነው ስለዚህ መጻሕፍቱ የሐሳብ አንድነት አላቸው ከእግዚአብሔር እንጂ ከሰው ፈቃድ እንዳልሆኑ እናውቃለን።
☞በተለይም በመጻሕፍቱ አንድነት ውስጥ የምናየው ስለ ክርስቶስ ያላቸው ምስክርነት ነው ለምሳሌ
ዘፍ፡-የሴቲቱ ዘር
ዘጸ፡-የፋሲካው በግ
ዘሌ፡-የመጨረሻው መስዋዕት
ዘኁ፡-የያዕቆብ ኮከብ
መዝ፡-መልካሙ እረኛ
ኢሳ፡-የሰላም አለቃ የዘላለም አምላክ የድንግል ልጅ
ኤር፡-የጽድቅ አምላክ
ዳን፡-የተቀባው(መሲሕ)
ሐጌ፡-የሁሉም ሕዝቦች ምኞት
ዘካ፡-የጌቶች ጌታ የአማልክት አምላክ
ሚል፡-የኪዳኑ መልእከተኛና የጽድቅ ፀሐይ
ማቴ፡-አማኑኤል የድንግል ልጅ
ማር፡-የእግዚአብሔር ልጅ፣የሰው ልጅ
ሉቃ፡-የመዳን ቀንድ
ዮሐ፡-ቃል፣የሕይወት ውሃ፣ትንሣኤና ሕይወት፣የዓለም ብርሃን፣የእግዚአብሔር በግ፣መልካሙ እረኛ
ሐዋ፡-የሚፈርደው
መልእክታት፡-ፋሲካችን፣የማዕዘን ድንጋይ፣የማይታይ አምላክ ምሳሌ፣አስታራቂ መስዋዕት፣በስጋ የተገለጠ
ራዕ፡-የይሁዳ አንበሳ፣አልፋና ኦሜጋ፣ፊተኛና ኋለኛ፣የሚያበራ የንጋት ኮከብ፣በብረት በትር የሚገዛ፣የአማልክት አምላክ የጌቶችም ጌታ፣የታመነው ምስክር ወዘተ
(የዮሐንስ ወንጌል 5)
----------
"46፤ ሙሴንስ ብታምኑት እኔን ባመናችሁ ነበር፤ እርሱ ስለ እኔ ጽፎአልና።
47፤ መጻሕፍትን ካላመናችሁ ግን ቃሌን እንዴት ታምናላችሁ?"
ስለዚህ በእግዚአብሔር መንፈስ ምሪት ስለተፃፉ የሐሳብ አንድነት ኣላቸው፡፡
(የሉቃስ ወንጌል 24)
----------
"44፤ እርሱም። ከእናንተ ጋር ሳለሁ በሙሴ ሕግና በነቢያት በመዝሙራትም ስለ እኔ የተጻፈው ሁሉ ይፈጸም ዘንድ ይገባል ብዬ የነገርኋችሁ ቃሌ ይህ ነው አላቸው።
45፤ በዚያን ጊዜም መጻሕፍትን ያስተውሉ ዘንድ አእምሮአቸውን ከፈተላቸው፤
46፤ እንዲህም አላቸው። ክርስቶስ መከራ ይቀበላል በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ይነሣል፥
47፤ በስሙም ንስሐና የኃጢአት ስርየት ከኢየሩሳሌም ጀምሮ በአሕዛብ ሁሉ ይሰበካል ተብሎ እንዲሁ ተጽፎአል።
48፤ እናንተም ለዚህ ምስክሮች ናችሁ።"
እንዳላቸው በወንጌልና በመልክታቸው ስለ ክርስቶስ ይመሰክራሉ፡፡ አጠር ባለ መልኩ ይህን ይመስላል።
☞የአሁኑ መጽሐፍ ቅዱስ ከድሮው በዘመን ሂደት ተበርዟል?
አልተበረዘም!!
መጽሐፍ ቅዱስ ሶስት ቅጂዎች ማለትም ዕብራይስጥ፣ ግሪክ፣ ሱርስት(ኣራማይክ) ቅጂዎች አሉት እነዚህ ቅጂዎች ቀዳሚ እንደ መሆናቸው በተለይም ግሪኩና ዕብራይስጡ ማመሳከሪያም ናቸው።በሌላ ቋንቋ ሲታተምም በነዚህ ሚዛንነት ነው።ወደ ሌላ ቋንቋ ተርጓሚው እንደ ትውልድ ቋንቋው ተናጋሪ(native speaker) ካልሆነ የትርጉም ክፍተት ሊፈጠር ይችላል።ከቀደምት መጻሕፍት ጋር በማስተያየት ግን በታተመው ላይ ያለው ልዩነት ይታወቃል።ስለዚህ እነዚህ ማመሳከሪያዎች ስላሉ ትርጉም ስራ ላይ የቃላት ለውጥ ቢፈጠር ይታረማል እንጂ ለመበረዝ ክፍተት የለውም።ጌታም እንዳለው ቃሉ ሕያውና የታመነ ነው አይሻርም አይበረዝም
"ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም" ማቴ24፥35
ምስጋና ለእግዚአብሔር ይሁን!!
BY የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት
Warning: Undefined variable $i in /var/www/tg-me/post.php on line 283
Share with your friend now:
tg-me.com/yemetshaf_qdus_tinat/5