Telegram Group Search
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (30)

15. የሰውን ነጻነት አክብር

አንዳንድ ገዥዎች ተነሥተው ነጻነት ሰጠናችሁ ይላሉ ። ሰው ለሰው ነጻነት መስጠት አይችልም ። የሰው ልጅ በተፈጥሮው ነጻነት ያለው ፍጡር ነው ። ደጋግ ነገሥታት ይህን ነጻነት ያከብሩ ፣ ያስመልሱ ይሆናል እንጂ ሊሰጡ አይችሉም ። የነጻነታችን ጌታ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ነጻነት ነጻ መሆን እንደ ልብ መፋነን አይደለም ። ነጻነት የሥጋን ፣ የነፍስን ፣ የመንፈስን መንሰራፋት ማክበር ነው ። ሰው ወደ ወደደው አገርና ግዛት ሂዶ መኖር ፣ መንቀሳቀስና መነገድ ፣ ማተረፍና መውለድ ይችላል ። ይህ የሥጋ ነጻነት ነው ። የነፍስ ነጻነቱ የማሰብ ፣ የመናገርና የመኖር መብት ነው ። የመንፈስ ነጻነቱ የወደደውን አምላክ የማመን ፣ የማምለክና የመደሰት ልዕልና ነው ። ነገሥታት ይህን ነጻነት በበላይነት መጠበቅና ማስጠበቅ ይገባቸዋል ። እኔ እንደማስበው አስብ ማለት ሳይሆን ወደ እኛ አሳብ ሰዎችን በፍቅርና በአመክንዮ መሳብ እርሱ ነጻነትን ማክበር ነው ። እኛ እንደምናምነው የማያምን ሰውን ላጥፋህ ልደምስስህ ማለት ከእግዚአብሔር ጋር መጣላት ነው ። ይህች ዓለም የሰዎችም የእንስሳትም ዓለም ናት ። የጋራ ዓለም ናትና በጋራ ጉዳይ አንድ እየሆንን የሌላውን የግል መብት ማክበር አለብን ።

ስለ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ብዙ ሰምተናል ፣ ብዙ ተናግረናል ። ዲሞክራሲ ባለመምጣቱም ኀዘን ገብቶናል ። የምንመኘውና ለዘመናት አትመጣም ወይ  ብለን የምንጣራው ዲሞክራሲ የሌላውን መብት ማክበር ነው ። የራስን ግዴታ አውቆ የሌላውን ድንበር አለመዳፈር እርሱ ዲሞክራሲ ነው ። የሰዎችን የማመን ፣ የመናገርና የመኖር መብት ማክበር እርሱ ዲሞክራሲ ይባላል ። ዲሞክራሲ እንደ ምርት ከውጭ አገር ተጭኖ የሚመጣ አይደለም ። ዲሞክራሲ በመካከላችን ያለ ከራስ ወዳድነት ወጥተን ስለሌሎች በማሰብ ተግባራዊ የምናደርገው ነው ። ለራሳችንና ለወገናችን የነፈግነውን ዲሞክራሲ ማንም ሊሰጠን አይችልም ። ሁልጊዜ ተሸማቀን ከመኖር አንድ ጊዜ ተስማምተን ነጻነትን ማስፈን ይገባናል ። በኑሮአችን ውስጥ ሁሉም ሰው የራሱን ነጻነት ማስከበር ይፈልጋል ። ዲሞክራሲ ግን የሌላውን ነጻነት ማክበር ነው ። ዲሞክራሲን ለማስፈን ሰው ከራሱ ውጭ የሚታገለው ነገር የለም ። የነጻነታችን ትልቁ ጠላት እኛው ነን ።

ሰዎች የተለያየ ፖለቲካዊ አመለካከት ይኖራቸዋል ። እንደ እኔ አስቡ ብሎ መጫን ግን አትኑሩ ብሎ መፍረድ ነው ። እንጨትና እንጨት ሲፋተግ እሳት ይወጣዋል ። የሰዎችም መነጋገርና መከራከር እውቀትን ይፈነጥቃል ። አንድነት ማለት አንድ ዓይነት መሆን አይደለም ። የተለያየን መሆናችን ውበትን እንጂ ጭንቀትን የሚፈጥር አይደለም ። ሰዎች የራሳቸው ሃይማኖት አላቸው ። ከምናምነው ተቃራኒ ነገር ቢያምኑም የመኖር መብት አላቸው ። በምንም መንገድ አገር የዜጎች እንጂ የአንድ ሃይማኖት መሆን የለባትም ። ይህ የዜጎችን መከራ ያበዛል ። የነገሥታትም ድርሻ ሃይማኖትን ማስፋፋት ሳይሆን ሰላምና ዕድገትን ማስከበር ነው ። ሰዎች በመሰላቸው መንገድ ራሳቸውን በተለያየ ሱስ እየጎዱ ሊሆን ይችላል ። መጥላትና ማሳደድ ግን አንችልም ። ወደ ቀናው መንገድ በፍቅር መመለስ እንችላለን ። በምድር ላይ ለሃይማኖት ሰው የተሰጠው ትልቅ መሣሪያ ፍቅር ብቻ ነው ።

አንተ ግን የሌላውን ነጻነት አክብር ። ፍላጎታቸውን ተጭነህ ወዳጆችህ የምታደርጋቸው የሉም ። ለጊዜው ያደፍጡ ይሆናል ፣ አቅም ሲያገኙ ግን ጥለውህ ይሄዳሉ ። ሰዎች የራሳቸው የሆነ ጊዜ ሊፈልጉ ይችላሉ ። ለፍላጎታቸው ተዋቸው ። ዛሬ አንተን ማግኘት አይፈልጉ ይሆናል ። ከራሳቸው ችግር ጋር እየታገሉ እንጂ አንተ ርካሽ ሰው ስለሆንህ አይደለም ። ሁለት ጊዜ ያህል ደውለህ መልስ ካልሰጡህ ተዋቸው ። ስላልፈለጉህ በማትፈለግበት ቦታ ጊዜ አታጥፋ ። አንተን የሚፈልጉህ “በመጣልኝ” ብለው የሚሳሱልህ ብዙ አሉ ። ሰው የሚጠሉትን ሲያሳድድ ፣ የሚወዱትን ይከስራል ። ራስህን ዝቅ ማድረግ ተገቢ ነው ። ራስህን ርካሽ ማድረግ ግን እንድትጣል ያደርግሃል ። በመገኘትህ የምትጠቅማቸው ሰዎች ይኖራሉ ፣ መገኘትህንና ቅርበትህን ካቃለሉ ግን ራቃቸው ። ክብር በሌለበት ፍቅር የለም ፣ ፍቅር በሌለበትም እግዚአብሔር የለም ። ማንንም ሰው አሳምን እንጂ አትለማመጥ ። የሰውነት ክፍሎችህ ካንተ ጋር ናቸው ። በሰው እጅ አትጎርስም ፣ በሰው ትንፋሽ አትኖርም ። የራስህን ሕይወት የሰጠህን ጌታ አክብር ።

ሰዎች የሚወድዱት አለባበስ ፣ የኑሮ ዘይቤ ፣ የቤት አሠራር ፣ የትዳር ምሪት ፣ የልጆች አስተዳደግ አላቸው ። ቋሚውን እውነት አሳውቃቸው እንጂ በእኔ መንገድ ካልሄዳችሁ እያልህ አትጎትታቸው ። የጣሉህ ሰዎች የጎተትካቸው እንቢተኞች ናቸው ። እገሌ ይጾማል አይጾምም ፣ እገሌ በቅድስና ነው ያለው በርኵሰት እያለህ በሰው ጓዳ አትዋል ። ይህ ርካሽነት ነው ። የራስህን ኑሮ ኑር ። ካንተ የሚፈልጉ ከሆነ እንኳን በወዳጆችህ በጠላትህም አትጨክን ። እንኳን አንተን ሰጪ አደረገህ ። የማይፈልጉ ሰዎችን ካልመከርኩ አትበል ። እርዳታህን የሚሸሹ ሰዎችን በግድ ካልረዳሁ አትበል ። የከበረውን ነገር ዋጋ በማይሰጡ ሰዎች ፊት አትጣል ። ውድ ጊዜህንም ተራ ነገርን ከሚፈልጉ ሰዎች ጋር አታባክን ። በማትፈለግበት ቦታ አትገኝ ። ምንም ነገር ስታደርግ ሰዎችን አስፈቅድ ። ያለ ፈቃዳቸው የምታደርገው ነገር ላንተም ለእነርሱም ደስታ አይሰጥም ። በጣም ጥንቃቄም ለስህተት ይዳርጋልና እጅግም ጠንቃቃ ፣ እጅግም ጻድቅ አትሁን ። ወደ ጓደኛህ ቤት እግር አታብዛ ። ወዳንተ ቤት እግር ቢያበዙ ግን ክርስቶስን እንደምትቀበል አድርገህ ተቀበላቸው ። የልብህን ሁሉ ፣ ለሁሉ አትናገር ። ሰዎችም ሁሉን እንዲነግሩህ አትፈልግ ። ባለትዳሮች ካልጋበዙህ በቀር ልዳኛችሁ አትበል ። ባልዬው በሌለበት ቤት ሚስቲቱ ብትቀጥርህ አትሂድ ።

በአገራችን በሰው ገላም ካላዘዝን የምንል ደፋሮች ነን ። የምንኖረውም በመጠባበቅ እንጂ ያመንበትን አይደለም ። በገዛ ሕይወታችን ላይ ድራማ የምንሠራ ምስኪኖች ነን ። ማኅበራዊነታችን መልካም ነው ። የሌላውን መብት መጋፋት ግን ነውር ነው ። በሁሉም ነገር ላይ አስተያየት መስጠት ግዴታችን ይመስለናል ። ለሁሉም መልስ አይሰጥም ። ብቻ የሰዎችን ነጻነት አክብር። ሊሄዱ የሚፈልጉትን በሰላም ሸኝ ። የሚመጡትን ደጎች ተቀበል ። በትዝታ ታስረህ የዛሬን ኑሮ አትሰርዝ ። ጨርሻለሁ ብለው መሄድ የማያውቁ ሰዎችን አጨራረሱን አሳያቸው እንጂ እንዲያውኩህ አትፍቀድላቸው ። ምክንያቱም ያንተ ኑሮ ይህ ነው ፣ እነርሱ ግን አማራጭ አላቸውና ። ርቀውህ የነበሩ ሰዎች እንደገና ሲመጡ በጥንቃቄ ተቀበል ። ምናልባት ያልጨረሱትን ተንኮል ለመጨረስ ይሆናል ። መጠንቀቅ ይቅር አለማለት አይደለምና ። ዕድሜህ እንዳያጥር ለአልምጦች ጋር አትኑር ! ከራስህ ጋር መሆን ጣፋጭ ነው ፣ ሰዎች ካልመጡ ሕይወትህ የተሰረዘ አይምሰልህ ! ሁልጊዜ ሰዎች አይገኙምና ከራስህ ጋር ልታደርግ የሚገባውን ዛሬውኑ አቅድ ! የምትፈልገውን በትክክል እወቅ ፤ ሕይወትህ መደሰት ትጀምራለች!

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 7 ቀን 2016 ዓ.ም.
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 21

ማር.4፥ 21 - 41

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 21

ማር.4፥ 21 - 41

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
እግዚአብሔር ይናገራል 3

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
እግዚአብሔር ይናገራል 3

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (31)

16. ዜማ

ዜማ በሰው ነፍስ ውስጥ የተቀመጠ ጥልቅ ፍላጎት ነው ። ዜማ ምድራዊውን ሰው ሰማያዊ የሚያደርግ ነው ። የነፍስ ሀልዎት መገለጫ ነው ። ነፍስ ስትታደስ ሥጋም አብሮ እንደሚታደስ ዜማ ይነግረናል ። ዜማ ሰዎችና እንስሳት የሚካፈሉት የጋራ ፍላጎት ነው ። ዜማ ሲሰሙ አደገኛ የሚባሉ አራዊት ይመሰጣሉ ። ዜማ ጨካኙን የማራራት አቅም አለው ። ቀሳውስት ቸገረኝ እንጂ ጨነቀኝ ሲሉ አይሰማም ። ጭንቀትም በጉልህ አይታይባቸውም ። የዚህ ምሥጢሩ ዜማ ነው ። ዜማ ያድሳል ። የከበደንን ደመና ያነሣል ። ዜማ ደስታን ፣ የአእምሮ መፍታታትን ፣ ጣዕምን ፣ ተደማጭነትን ፣ ተወዳጅነትን ያጎናጽፋል ። በዜማ ውስጥ ብዙ መልእክቶች አሉ ። ዜማ ምስጋናንና ትምህርትን በጣዕም ለማስተላለፍ የሚረዳ ነው ። ዜማ የታላቅ ፍልስፍና መገለጫ ነው ። ዜማ በሰማይ የሚጠብቀን ድግስ ነው ። ቅዱስ ያሬድ የዜማው ባላባት እስከ ዛሬ ድረስ ተሰምተው የማይጠገቡ ዜማዎችን ለቤተ ክርስቲያን አበርክቷል ። በርግጥ መንፈሳውያን እንደ መሆናችን እግዚአብሔር እንደ ገለጠለት እናምናለን ፤ የስጦታውን ምንጭም አንስትም ። ቅዱስ ያሬድ እንዲህ ተቀብሮ መቅረቱ ኢትዮጵያዊ መሆኑ ነው ። የሌላው ዓለም ሀብት ቢሆን ኖሮ የየቀኑ ርእስ ይሆን ነበር ።

ዜማ የትልቅ ሥልጣኔ መገለጫ ነው ። ዜማን በኖታ ዓለም ከማቅረቡ በፊት ቅዱስ ያሬድ አዘጋጅቶታል ። ዜማ ቋንቋ ነው ። ስብሐተ እግዚአብሔር የሚደርስበት ሰረገላ ነው ። ዜማ ክንፍ ነው ፣ ወደ ሰማየ ሰማያት የምንወጣበት ነው ። ጸሎታችንን በዜማ ብናደርስ የምንጸልየውን እናስተውለዋለን ፣ እንባ በዓይናችን ይሞላል ፣ ልባችን በመለኮት ፍቅር መቅለጥ ይጀምራል ። ጮክ ብለን ማዜምና መዘመር በጣም ወሳኝ ነው ። በሳምንት አንድ ቀን እንኳ አፍ አውጥተን ብናዜም የከበደን ነገር ይቀለናል ። ዜማ የነፍስ ምግብ ፣ የጭንቀት ዱላ ነው ። ማንጎራጎር የሚወድዱ ሰዎች ደስተኞች ናቸው ። እያንጎራጎሩ ሲያለቅሱ ይታደሳሉ ። እንባ ወደ ውጭ ካልፈሰሰ ወደ ውስጥ ይፈሳል ። ያን ጊዜ ሰባራ ሰው ያደርገናል ። ዜማ ስብሐተ እግዚአብሔር የሚቀርብበት መሠዊያ ነው ። እግዚአብሔርን የሚማርከው ዜማው ሳይሆን የልባችን መቃጠል ነው ። ዜማ ግን ምድራዊነታችንን ሰማያዊ ያደርገዋል ።

የሚያዜሙ ሰዎች ብዙ ጊዜ እውቀት አይወድዱም ። በዚህ ምክንያት “ድምፅና ቁንጫ ባዶ ቤት ይወዳል” እየተባሉ ይተቻሉ ። የሚያዜም ሰው ግጥም ፣ ቅኔ ፣ የንግግር ችሎታን ማዳበር አለበት ። በርግጥ የሊቃውንቱን ቅኔ ለዓለም የሚያደርሱት ዜመኞች ናቸው ። የሚያዜሙም ከእውቀት መራቅ አይገባቸውም ። ዜማ ሙያ ሲሆን ለጥቂቶች ነው ። አምልኮ ሲሆን ግን ለሰው ልጆች ሁሉ ነው ። አእዋፋት በማለዳ ያዜማሉ ። ባናያቸውም እንወዳቸዋለን ፣ ዜማ እንደሚያነቃም እንረዳለን ። የሚያዜሙ ሰዎች በሰው ነፍስ ውስጥ አሉ ። ሰው ከውጫዊ አካሉ ይልቅ ነፍሱ ስፋት እንዳላት ዜማና ተጽእኖው ይገልጥልናል ። ዜማ የተለያየ መልእክት አለው ብለናል ። የማኅበረሰብ መግባቢያ ቋንቋ ነው ። ሰርግን ፣ ጦርነትን ፣ ደስታን ፣ ኀዘንን በዜማ እንወጣለን ። ሥርዓት ያላቸው ዜማዎች ፣ የማኅበረሰቡ ግኝት የሆኑ ግጥሞች ለሰርግ መዋል አለባቸው ። ዜማ የዝሙት ማስታወቂያ ሲሆንና እጅና እግርን ማወደሻ ሁኖ ሲቀር ይተቻል ። መንፈሳዊነት ማኅበረሰብን የሚደፈጥጥ አይደለም ። በሰርጌ ጌታ ይክበር የሚሉ አሉ ፣ ጥሩ ነው ። ጌታ ግን የሚከብረው በሁለት ሰዓት ፕሮግራም ብቻ ሳይሆን በኑሮ ውስጥ ነው ። ሚስትህን በአጋፔ ፍቅር ስትወዳት ፣ ባልሽን እንደ ራስ ስታከብሪው ያን ጊዜ እግዚአብሔር ይከብራል ።

በዜማ መለቀስ ፣ ኀዘን መተንፈስ አለበት ። ያልወጡ ኀዘኖች ብዙዎችን ለድባቴ እየዳረጉ ይገኛሉ ። አገራችን ታላላቅ ሰዎች የነበሩባትና ያሉባት አገር ናትና ደስታንም ኀዘንንም መግለጫ አበጅተዋል ። ደግሞም የባሕላችን ማሳያ ነውና ሊከበር ይገባዋል ። አለማልቀስ ዘመናዊነትም መንፈሳዊነትም አይደለም ። ሬሳ አስቀምጦ አላለቅስም ማለት ጉራ ሲሆን አብረው የሚያላቅሱ ሲሄዱ ውጋቱ ይጀምራቸዋል ። እንዴት ሰው ሞትን እያስተናገደ ለማልቀስ ይሳሳል ?

አገርን የሚያወድሱ ፣ ጀግንነትን የሚያነሣሡ ዜማዎች አንድን ትውልድ የአገር ዘብ አድርጎ የማቆም አቅም አላቸው ። እዚህ የምንጽፈውና የምናመልከው በዳር ድንበር የሚጠብቅ ወታደር ስላለ መሆኑን ማወቅና ክብር መስጠት ይገባናል ። ከዜማ ጋር የዜማ መሣሪያዎችን መለማመድ ግድ ይላል ። ቢያንስ አንድ የዜማ መሣሪያ ማወቅ ለቀጣዩ ዕድሜ ፣ ለእርጅና ብቸኝነት ወሳኝ ነው ። ዜማ ለማኞች እንኳ ጨካኙን የሚያራሩበት ነው ። የዜማ ዕቃ ይዘው የሚያዜሙም ከመንገዳችን ቆም ያደርጉናል ። ዘወትር ከጸሎታችን ጋር ድምፅ አውጥተን ብንዘምር ላሉብን ውጥረቶች ቅለት ይሰጠናል ። ነገር ግን አጠገባችን ያለውን ሰው እንዳንረብሽ ፣ ተወዳጁን አምላክ በእኛ ረባሽነት እንዳናስጠላው መጠንቀቅ ያስፈልጋል ። ዜማ የራሱ ሥርዓት አለውና ሊጠና ፣ ሊያድግና ሊበረታታ ይገባዋል ። ከሕይወት ሥነ ሥርዓት አንዱ ዜማ ማዜም ነው ። በቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት የዜማ ዕቃ ጸናጽል ፣ መቋሚያና ከበሮ ነው ። የምእመናን የዜማ ዕቃ በገና ፣ መሰንቆ ፣ ክራር ፣ እንዚራ ተጠቃሽ ናቸው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 10 ቀን 2016 ዓ.ም.
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (32)

17. ማኅበራዊ ኑሮ ይኑርህ

አንድነትን በሚመለከት አራት ዓይነት ኅብረቶች አሉ ። የመጀመሪያው ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ያለው አንድነት ነው ። ሁለተኛው ሰው ከራሱ ጋር ያለው አንድነት ነው ። ሦስተኛው ሰው ከሰው ጋር ያለው አንድነት ነው ። አራተኛው ሰው ከአማኝ ጋር ያለው አንድነት ነው ። ከእግዚአብሔር ጋር ያለን አንድነት እርሱን በማወቅ ፣ በማምለክና ትእዛዛቱን በመፈጸም ፣ በንስሐ በመታደስ ላይ የተመሠረተ እንዲሁም የሚቀጥል ነው ። ሰው ከራሱ ጋር ያለው አንድነት ከእግዚአብሔር ጋር ባለው አንድነት ላይ የሚመሠረት ነው ። ሰው ከራሱ ጋር መለያየት ካመጣ ፣ ውስጣዊ ግጭት ካለበት ሰላምና ደስታ እንዲሁም የመኖር ፍላጎት እየራቀው ይመጣል ። ሰው ከሰው ጋር ያለው አንድነት ከራሱ ጋር ባለው አንድነት መሠረት ላይ የሚቆም ነው ። ከራሱ ጋር አንድ ያልሆነ ከሌላው ጋር አንድ ሊሆን አይችልም ። ሰው በማመን እርሱን ከሚመስሉት ጋር አንድ የሚሆንበት ዘላቂ አንድነት አለ ። ይህን አንድነት ልዩ የሚያደርገው በሰማይም የሚቀጥል በመሆኑ ነው ።

አማኒ የሆነው ወንድማችን ዘመዳችን ፣ ጎረቤታችን ፣ የቅርብ አገልጋያችን ላይሆን ይችላል ። ያለን ግንኙነት መንፈሳዊ ነው ። ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም እንድንኖር መጽሐፍ ያዝዘናል (ሮሜ. 12፡18)። አንዳንዴ አዳጋች ይሆናልና ቢቻላችሁስ የሚል ሚዛን ያስቀምጧል ። ከተቻለን ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም መኖር መልካም ነው ። ሰዎች ግን የእኛ እምነትና ህልውና እየረበሻቸው ሊጣሉን ይችላሉ ። ክርስቲያን በምንም መንገድ ሌላውን የሚያውክ ሊሆን አይችልም ። እርስ በርሳቸው የዘረኝነት ችግር ቢኖርባቸውም ጌታችን ግን ከአይሁድ ወገን ተወልዶ የሳምራውያን ወዳጅ ነበረ ። ሰው ያገለላቸውን ቀራጮችና አመንዝሮች ከእርሱ ጋር አብረው እንዲበሉ ይጋብዛቸው ነበር ። ክርስቲያን ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር መስፈርት የሚያደርገው ሃይማኖቱን ወይም እንደ እኔ ካላመኑ የሚለውን አመለካከት አይደለም ። ክርስቲያን በመጽሐፍ እንጂ በሰይፍ የሚያሳምን አይደለምና ።

ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር መዋሸት አለብን ማለት አይደለም ። ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር የራሳችንን አመለካከትና ሃይማኖት እያከበርን የሌሎችንም ማክበር ነው ። የሃይማኖትህ መሪ የሆነው አባት ከቡዲስት ወይም ከአረሚ ጋር ሰላም ሲባባል ስታይ የምትበሳጭ ከሆነ ይህችን ዓለም ያንተ እምነት አባላት ብቻ እንዲኖሩባት እየፈለግህ ነው ። የራስን ይዞ የሌላውን ማክበር ይቻላል ። ሰዎች ያመኑበትን በጥላቻ ለማስጣል ስንሞክር የበለጠ እንዲያከሩ እናደርጋቸዋለን ። ምንም ውክልና የሌላቸው ለቤተ ክርስቲያን መልስ እንሰጥላታለን የሚሉ ወጣቶች በየጊዜው በሃይማኖት ስም ጥላቻን ሲዘሩ ይታያሉ ። እዚህ ያለውን አይሁድ ስትነካው ኢየሩሳሌም ያለው ክርስቲያን መኖሪያ ያጣል ። ሁሉም አገር አለውና ። እዚህ ያለውን ሙስሊም ስትነካው ግብጽ ያለው ክርስቲያን መሸበር ይጀምራል ። የዚህች ዓለም ሰላም የቆመው በሰው ልጆች ሁሉ ነጻነት ላይ ነው ። የራሱ እምነት ያሳረፈው ሰው የሌላውን በመንቀፍ ጊዜውን አይፈጅም ።

ማኅበራዊ ኑሮ በመከባበር ላይ የተመሠረተ ነው ። ማኅበራዊ ኑሮ በብዙ መንገዶች ሊጎዳ ይችላል ። የብቸኝነትና የጭንቀት መንፈስ ሲታገለን ማኅበራዊ ኑሮአችን እየተጎዳ ይመጣል ። መሸሽን ገለል ብሎ መቀመጥን እንወዳለን ። አንዳንድ ጊዜም ከትዳራችንና ከልጆቻችን መሸሽ ይታየናል ። የብዙ ትዳር ችግር ማንም ያላወቀው ጭንቀት ነው ። መነጫነጩ ፣ ስካሩ ውጤት ነው ። መነሻው ግን ጭንቀት ነው ። ሥሩን ካልፈወስን ቅርንጫፉ አይድንም ። ስለ ሰዎች ያለን ተገቢ ያልሆነ አመለካከት ይኖራል ። ይህ ከቤተሰብ ፣ ከአስተዳደግና ከደረሰብን ጉዳት የተነሣ የሚመጣ ነው ። በዚህ ምክንያት ከማኅበራዊ ኑሮ እንርቃለን ። ልጆች ሲያድጉ ከሰው ጋር እንዲቀላቀሉ ፣ ሰርግም ልቅሶም እንዲያዩ ተደርገው ሊሆን ይገባል ። ዛሬ ብንሸፍናቸው ነገ ብቻቸውን ይጋፈጡታል ። ልጆችን ተክቶ የሚኖር ወላጅ ሞቱን የረሳ ወላጅ ነው ። ዘመናዊነት ማኅበራዊነትን እየናደ ነው ። የትዳር ክፍተቶች ፣ የፍቺ መበራከቶች ማኅበራዊነትን ይጎዳሉ ። የሚሰሙና የሚታዩ ዘግናኝ ወንጀሎች ሰውን ፈሪ በማድረግ እንዲራራቅ ያደርጉታል ። ወንድ ልጃቸውን ለሴትም ለወንድም አደራ ብለው ለመሄድ የተቸገሩ ወላጆች አሉ ። የሚሰሙት ነገር ሕሊናቸውን አርክሶታል ፣ ልባቸውን ፈሪ አድርጎታል ። የገዛ ሴት ልጃቸውን ለአባት ትተው መሄድ የሚፈተኑ እናቶችን እናውቃለን ። ማኅበራዊነት በአባትና በልጅ መካከል ከፈረሰ ሌላ ቦታ መጠበቅ ከባድ ነው ።

ዘመናዊው ዓለም የግል የሆኑ ነገሮችን በማብዛት አንድነትን የማፍረስ ዘመቻ ላይ ነው ። በየጊዜው በላቦራቶሪ ተመርተው በሚለቀቁ በሽታዎች ሰው ሰውን እንዳይቀርብ ሰይጣናዊ ተልእኮአቸውን እየተወጡ ነው ። በዚህ ምክንያት የሰው ልጅ በብቸኝነት ዕድሜው እያጠረ ይመጣል ። ማኅበራዊነት ዕድሜን ይቀጥላል ፣ ደስታንም ይሰጣል ። አብረው ካልበሉ ፣ አብረው ካልተደሰቱ ፣ አብረው ካላለቀሱ የዚህ ዓለም ኑሮ ሊገፋ አይችልም ። ራስ ወዳድነትና ስስት ፣ ሁሉንም ነገር ስሌት ውስጥ ማስገባት የማኅበራዊነት ጠላት ነው ። ለሌሎች ስንኖር ሌሎች ለእኛ ይሞቱልናል ። የምናጭደው ከዘራነው በላይ ነውና ። ደግሞም ውጤቱን በማሰብ ሳይሆን በራሱ ትልቅ ደስታ በመሆኑ ማኅበራዊነት ሊጠነክር ይገባዋል ። አንተም ማኅበራዊነት አስፈላጊህ ነውና የሠራኸውን የግል ደሴት አፍርሰህ ከሰው ተቀላቀል ! ሞኝ አትሁን ከምትሰጣቸው የሚሰጡህ ይበልጣል ! ፌስ ቡክ ላይ ልቅሶ መድረስ ፣ ቲክ ቶክ ላይ ሙሾ ማውረድ ቁምነገር አይምሰልህ ፣ የቀኑ የወሬ ጥማትህ ማሟያ ወይም ምን ላውራ ለሚለው ጭንቀትህ ማረፊያ ነው ! ማኅበራዊነት አካላዊነት ነው ! መሄድ ፣ ጊዜ መስጠት ፣ አቅፎ ማጽናናት ፣ በጎደለው መሙላት ነው !


ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 14 ቀን 2016 ዓ.ም.
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 22

ማር.5፥ 1 - 20

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 22

ማር.5፥ 1 - 20

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
እግዚአብሔር ይናገራል 4

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
እግዚአብሔር ይናገራል 4

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (33)

18. ስፖርት

ከሕይወት ሥነ ሥርዓቶች አንዱ ስፖርት ማዘውተር ነው ። ለታላቁ ሩጫ በዓመት አንድ ጊዜ መሮጥ ፣ ለፎቶ እንጂ ለጤና ምንም ጥቅም የለውም ። የሰውነት እንቅስቃሴ ዕለታዊ ግዳጅ ነው ። እጅ ለመሥራት ፣ እግር ለመራመድ እስከ ተሠራ ድረስ መሥራትና መንቀሳቀስ አስፈላጊ ነው ። አሊያ የሞት ጎረቤት ፣ የበሽታ ዳስ ሆኖ መኖር ነው ። “መቀመጥ ቆመጥ ነው” እንዲሉ ። ዘመናዊነት ከጎዳን ነገር አንዱ የስንፍና ሠራዊት ማብዛቱ ነው ። ከምግብ እንኳ የሚታኘክ አንፈልግም ። በፋብሪካ ተቀነባብሮ ፣ ልሞ ፣ በሚሳብ መልክ መውሰድ ነው ። ይህ ጥርስ ያላወጡ ፣ ምግብ ያለመዱ ሕፃናት ይወስዱት የነበረ ነው ። ተፈጥሮአዊ ሂደቱን ጠብቆ ምግብን መመገብ ብዙ ጥቅም አለው ። መዓዛውን ፣ ጣዕሙን እንድናውቅ ያደርገናል ። ጥርሳችን ጥንካሬ ያገኛል ። ምግብን የሚፈጀው የአካል ክፍልም እየመጣ ላለው የምግብ ዓይነት ዝግጅት ያደርጋል ። ከጠዋት እስከ ማታ ከመቀመጫቸው የማይነሡ የቢሮ ሠራተኞች አሉ ። ሻይ ቡና እዚያው ጠረጴዛቸው ላይ ይመጣላቸዋል ። በየተቋማቱ ሻይ ቡና በእግር ተጉዘው ከሚጠጡበት ቦታ መዘጋጀት አለበት ። አንድ ተቋም የሠራተኞቹን ጤና መጠበቁ ለራሱም ህልውና ወሳኝ ነው ። መንግሥት በከፍተኛ ሁኔታ ሆስፒታሎችን መገንባት ሥራው ነው ። መድኃኒት በውጭ ምንዛሪ ወደ አገር ያስገባል ። ዜጎችም ከአገር ወጥተው በውድ ገንዘብ ይታከማሉ ። በዚህም ውጤቱ አነስተኛ ነው ። የስፖርት ማዘውተሪያዎች በየሰፈሩ ቢገነቡና ጤናማ ማኅበረሰብ መገንባት ቢቻል የአገር ወጪ ይተርፍ ነበር ። ችግርን ከሥሩ መከላከል ውጤታማ ያደርጋል ።

በአገራችን የአንድ ትልቅ ቤተሰብ የልጆች አስተዳደግ የሚያሟላው አራት ነገሮች ነበሩ፡- ትምህርት ፣ ግብረ ገብ ፣ ስፖርትና የዜማ መሣሪያ ማወቅ ናቸው ። ትምህርት ስለ ራሱና ስለሚኖርበት ዓለም ግንዛቤ ይሰጠዋልሰ ። ግብረ ገብ ከራሱና ከሰዎች ጋር የሚኖርበት ትልቁ የመኖሪያ ፈቃድ ነው ። “የሰው አገሩ ምግባሩ” እንዲሉ ። ስፖርት ንቃቱን ፣ ጥንካሬውን የሚጠብቅበት ነው ። የዜማ ዕቃ ፈጣሪውን የሚያመሰግንበት ፣ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚያደርስበት ነው ። ይልቁንም ዕድሜ እየገፋ ሲመጣ ወዳጅ እያነሰ ይመጣልና የዜማ ዕቃ ጓደኛም ነው ። የሰውነት እንቅስቃሴ ከተሟላ አስተዳደግና አኗኗር የሚደመር ነው ። በዚህ ዘመን ስፖርት የሚመለከቱ ብዙ የዓለም ሕዝቦች አሉ ። እንደውም አንድ አባት እንዳሉኝ “ከእግዚአብሔር በላይ ኳስ ተከታይ አለው ።” ኳስ መመልከቱ ያን ያህል ስህተት አይደለም ። ከአምልተ እግዚአብሔር ፣ ከትዳራችን ፣ ከማኅበራዊ ግዳጃችን ከበለጠብን ግን አደገኛ ጣዖት ነው ። “የመጀመሪያውን ስብከት ለእኔ ስጡኝ ፣ የማንቸስተር ጨዋታ አለብኝ” ያለ ሰባኪ እንዳለ ሰምተናል ። እነዚህ የሚያስተምሩት በሥጋ በነፍስ ቢደነቁር አስደናቂ አይደለም ። ቤተ ክርስቲያን የሚቆጭላት አጥታ ቁማር መጫወቻ ከሆነች ቆይታለች ።

ስፖርት ማድነቅና ስፖርት መመልከት ለጤናችን ምንም የሚያደርገው አስተዋጽኦ የለም ። የሚደግፉት ቡድን በመሸነፉ ራሳቸውን ያጠፉ ወጣቶችን በቅርብ ጊዜ ሰምተናል ። የድሀን ቅብጠት የሀብታም አገር በጀት አይችለውም ። ለእውነቱ ካየነው በአገራችን መወራት ያለበት ሰው ስለ መሆን ፣ እንጀራ ስለ መብላት ፣ ስለ ንጽሕናን አጠባበቅ ነው ። የሚገርመው ስፖርት አድናቂዎች ጠጪዎች ናቸው ። የሰውነት ቅርጻቸው የተበላሸ ነው ። የሚደግፉት ቡድን ካሸነፈ በደስታ ይጠጣሉ ፣ ካላሸነፈ በንዴት ይጠጣሉ ። የስፖርት ደጋፊዎች ግብ መጠጥ መጠጣትና ለመጠጡ ምክንያት ማበጀት ነው ። የምናደንቃቸው ስፖርተኞች በብዙ ሚሊየን ዶላር የሚከፈላቸው ሲሆኑ ለእነርሱ ሥራቸው ነው ። እነርሱ ኢትዮጵያ የምትባል አገር መኖርዋን እንኳ አያውቁም ።

ስፖርት የምንሠራው ለተስተካከለ ቅርጽ ቢሆንም ፣ ቅርጻችንን ስናሳይ ለመዋል ግን አይደለም ። ይህ ራስን ማምለክ በመሆኑ በበሽታና በውድቀት ሳይቀጣ አይቀርም ። እዩኝ እዩኝ ያለ ገላ ደብቁኝ ደብቁኝ ይላል ይባላል ፤ ደግሞም እውነት ነው ። ይህ ሕግ ነው ፣ የገዛ አካላችንም ጣኦት ሆኖብን ላስመልክ ካልን በቍስል ይመታል ። ዛሬ ቅርጻቸውን አሳምረው ሀብታም ሴት የሚጠብቁ ድኩማን ወንዶች እያመረትን ነው ። ኤልያብ ተቀምጦ ዳዊት ለንግሥና የተመረጠው ቁመና መስፈርት ስለማይሆን ነው ። ቁመና እያዩ ሹመትና ማዕረግ የሚሰጡ አባቶች አሉ ። ይህ አዲስ አይደለም ነቢዩ ሳሙኤልም የተታለለበት ነው ። “እግዚአብሔር ግን ሳሙኤልን፦ ፊቱን የቁመቱንም ዘለግታ አትይ ሰው እንዲያይ እግዚአብሔር አያይምና ናቅሁት ሰው ፊትን ያያል፥ እግዚአብሔር ግን ልብን ያያል አለው።” (1ሳሙ. 16 ፡ 7) ። ቁመናን እያያችሁ ባል የምታስሱ እኅቶች ከተሰናዱ ሌቦች ራሳችሁን መጠበቅ አለባችሁ ። ሰው ስፖርት የሚሠራው ለራሱ ነው ። ስለዚህ እዩልኝ እያሉ ቪዲዮ መልቀቅ ምን የሚሉት ነገር ነው ? መጽሐፍ እያነበበ ቪድዮ የሚለቅ የለም ። የመጀመሪያው መጽሐፍን እንደ እርግጠኛ ጠላታችን ነው የምናየው ። ሁለተኛው መጽሐፍ የሚያነብ ሰው እዩልኝ ስሙልኝ የሚል ኑሮ የለውም ። ራስን የመሸጥ ግርግር ውስጥ ያለው ይህ ዘመን በድሀ ሕዝብ ፊት ቍርሳቸውን እየበሉ የሚለቅቁ ፣ መኖር ባቃተው ወገን ፊት እየተገላበጡ ከየጂሙ ፎቶ የሚሰድዱ ጨካኞችን ያፈራ ነው ።

አንተ ግን የሰውነት እንቅስቃሴ አድርግ ። ግድ ጂም መግባት አያስፈልግህም ፣ የራስህ ሰውነት የስፖርት መሥሪያም ነው ። ታክሲ ለመጠበቅ አንድ ሰዓት ከመቆም አንድ ሰዓት ተራምደህ እቤትህ ግባ ። በየጂሙ ያለው ወሬና የነጋዴዎች ትውውቅ ፣ ለመቼ ቀን እንደሆነ ባይታወቅም የሰቡ ጎረምሶች የሚታዩበት ነው ። ሌላው ይሥራልኝ ብለህ የተውከው ተግባርህ በራሱ ስፖርት ነው ። ከተፈጠርንበት ሥሪት እየራቅን ስለሆነ ታላቅ የጤናና የሥነ ልቡና ጉዳት ውስጥ ገብተናል ። አንተ ግን በየቀኑ ቢያንስ ለአንድ ሰዓት ያህል የእግር ጉዞ አድርግ ። ከመኝታህ ከመነሣትህ በፊትና በተነሣህ ጊዜ መንጠራራት ፣ ሰውነትህን ማፍታታት አትርሳ ። የትንፋሽ ስፖርት ብቻ ሳይሆን የጥንካሬ ስፖርቶችንም ልመድ ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 17 ቀን 2016 ዓ.ም.
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (34)

19. ጨዋታ ልመድ

ጨዋታ ማለት ጨዋዊ ፣ ጨው የሆነ ፣ ጣዕም ያለው ፣ ንግግርን የሚያጣፍጥ ፣ ተወዳጅ የሚያደርግ ማለት ነው ። ጨዋታ የጨዋ ሰው ስልት ፣ ሌላውን ለማስደሰት የሚደረግ ቅዱስ መንገድ ነው ። ሰዎች ሰዎችን ለማስደሰት ያሰክራሉ ፣ ለዝሙት ይዳርጋሉ ። ጨዋታ ግን የጨዋ ሰው መንገድ ሲሆን በቅዱስ ነገር ያንን ሰው ማስደሰት ነው ። ቀንበር የበዛበት ይህ ዓለም ያለ ጨዋታ አይዘለቅም ። እስከማውቀው ካህን ችግረኛና ረሀብተኛ ነው ። ዛሬ ላይ የሚታዩ ጥቂት መሳፍንት አከል ካህናት ቢኖሩም አሁንም ድረስ ካህን ኑሮው የጭንቅ ናት ። ካህን ከአገልግሎት መልስ የሚያገኛትን ጥሬ በጨዋታ ጮማ ያደርጋታል ። ጨዋታው ስልት አለው ። የራስንም ክብር መጠበቅ አለውና ነውረኛ ቃላት አይነገሩበትም ። ያ ሰው ስለ ራሱ ይነገረዋል ፣ የሚነገረው ግን ራሱ የሚስቅበትን ክስተት ነውና ይስቃል ። ካህን ያንን የችግር ዘመን በጨዋታ አጣፍጦታል ። ጨዋታ ሰው ራሱን የሚያክምበት ትልቅ ፈውስ ነው ። የሰው ልጅ በመተንፈስ የሚኖር ፍጡር ነው ። ሲተነፍስ የተቃጠለው አየር እየወጣ አዲሱ ይገባል ። ሲጫወትም ብሶቱ እየተነነ ተስፋ በውስጡ እየሞላ ይመጣል ።

መጫወት በፍቅር መሠረት ላይ የሚታነጽ የደስታ ቤት ነው ። ለመጫወት መፋቀር ፣ መጣጣም ፣ መቀራረብ ፣ አብሮ መኖር ፣ መገጣጠም ፣ መፈቃቀድ ያስፈልጋል ። ጨዋታ ፀጥታን ይሽራል ። በዓለም ላይ በገንዘብ የሚገዙ ፀጥታዎች አሉ ። ሰዎች የጽሞና ቦታዎችን ፣ ውድ ሆቴሎችን የሚመርጡት ጸጥታን ለመግዛት ነው ። አስፈላጊ ጸጥታዎች አሉ ። ሰውን ከችግሩ ጋር እንዲያወራ ፣ እንዲተክዝ ፣ ውስጡ እንዲያልቅ የሚያደርጉ ጸጥታዎችም አሉ ። መንፈሳዊነት ማለት ማኩረፍ ፣ ወይም ሁሉንም ነገር እየገሠጹ መሄድ አይደለም ። መንፈሳዊነት ራስን ማስጨነቅ ሳይሆን ራስን መካድ ነው ። ራስን ማስጨነቅ ስቃይን መጋበዝ ነው ። ራስን መካድ ግን ራስን በቅጡ መመልከት ፣ ቀለል አድርጎ መኖርና ኅብረት መፍጠር ነው ። ጨዋታ አጉል ጸጥታን ይሽራል ። ሰዎች የሚወለዱትም የሚሞቱትም አንድ ቀን ነው ። አንድ ቀንና አንድ ሰዓት ዋጋው ብዙ ነው ። ይህችን ሰዓት ማለፍ ባለመቻል ብዙዎች ራሳቸውን ለአደጋ አጋልጠዋል ። ስንጨነቅ ለአንድ ሰዓት ከሚያጫውተን ወዳጅ ጋር ማሳለፍ መልካም ነው ። ልብ አድርጉ በቅጽበት ስህተት ሾፌር ራሱንም ሰዎችንም ይገድላል ። በቅጽበት ትዕግሥት ማጣት አንድ ሰው ዕድሜ ልክ እስራት ይገጥመዋል ። የጨዋታ ሰዓቱ ትንሽ ቢሆን እንኳ የሚያሳልፈው ነገር አለ ።

በአገራችን በመንገድም ይሁን በቤት ፣ ሰው ከሰው ሲገናኝ ሰላምታ ይሰጣጣል ። ሰላምታ ለመሰጣጠት መተዋወቅ መስፈርት አልነበረም ። ዛሬ እንዲሁ መቀላቀል ፣ ዘመናዊ ኩርፊያ በዝቷል ። ስለዚህ ላያችን ጨርቅ ደርቦ ውስጣችነ ተራቁቷል ። ጨዋታ ግን ኑሮን ያቀላል ። በመንገድም ጨዋታ ካለ መንገዱ ያጥራል ። በተለያዩ መዝናኛዎች ጨዋታ ካለ ሰውዬው የከፈለውን በትክክል መጠቀም ይችላል ። ጨዋታ የወሬ ቅመም ፣ የኑሮ መርዝ ማርከሻ ፣ ሰውና ሰው የልብ ስጦታ የሚለዋወጡበት ነው ። አንዳንድ ሰዎች ራሳቸውን ደረቅ አድርገው ገንብተውታል ። ስለዚህ ሲናገሩ እንኳ የሚጠቀሙአቸው ቃላት ሥራ ላይ መዋል የሌለባቸው እንደሆኑ እያሰብን ለእነርሱ እናፍርላቸዋለን ። ጨዋታ የሚያውቅ ሰው ግን ብዙ ከመናገር ንግግሩ የጠራ ይሆናል ። መናገር ባያስፈልግ ኖሮ አንደበት ባልተፈጠረ ነበር ። የተከለከለው ማውራት ሳይሆን ሁሉን መናገር ነው ፣ መጫወት ተገቢ ነው ። “የዘመድ ጨዋታ ቆራጣ ቆራጣ” እንዲሉ ! ርእስ የለውም ፣ አጀንዳ አይያዝም ፣ ብዙ ነገሮችን ይነካካል ፤ ግን ደስ ይላል !

ሰዎች እንስሳትን የሚያረቡት አንዱ ለመጫወት ነው ። እንስሳት ያጫውታሉ ፣ ያነጋግራሉ ። ዝም በማለት አእምሮ በድን እንዳይሆን ዶሮ በየሰዓቱ እሽ ሲሏት ፣ ውሻን ተዉ ሲሉት ፣ ድመት ክፍ ስትባል ጨዋታ ይኖራል ። የሰውን ልጅ ብቸኝነት እየተካፈሉ ያሉ ፣ ይበልጥ በሰለጠነው ዓለም እንስሳት ናቸው ። የሚገርመው ሰው ለሰው ያለው ግንኙነት ፈርሶ ሰውና እንስሳት የጠበቀ ግንኙነት ጀምረዋል ። በአሜሪካ ምድር ዓመታዊ የውሻ በጀት ኢትዮጵያ ለሕዝብዋ እስካሁን መድባው አታውቅም ። ባል አለኝ ፣ ልጅ አለኝ ወይም ውሻ አለኝ የሚል መልስ በዘመናዊው ዓለም ተለምዷል ። ሥልጣኔው ትዳርን በወራት ዕድሜ ውስጥ አስገብቶታል ። በትዳር ቢያንስ ሦስት ዓመት ብቆይ ነው ፣ እርሱም ከተሳካ ፣ ከውሻዬ ጋር ግን አሥራ ሁለት ዓመት እቆያለሁ እያሉ ከሰው ውሻ መምረጣቸውን ይናገራሉ ። ሰው ጨዋታ ፣ አነጋጋሪ ይፈልጋል ።

ጨዋታ የሚያውቁ ሰዎች ምነው በመጡ የሚባሉ ናቸው ። እነዚህ ሰዎች የሰውን ጭንቀት ያለ ኪኒን ለማስወገድ የሚጥሩ ናቸው ። የጎንዮች ጉዳት የሌለበት የአእምሮ መድኃኒት ጨዋታ ይባላል ። ጨዋታ ለማወቅ ማንበብ ፣ ታሪክ ማወቅ ፣ ትልልቅ ሰዎችን መጠየቅ ፣ ተጨዋቾችን ማዳመጥ ይገባል ። ልብ አድርጉ ጨዋታ ማለት ሐሜት ፣ ሽሙጥ ፣ ሌላውን ዝቅ ማድረግ ፣ አሽሙር ፣ በጎን ሰውን መውጋት በፍጹም አይደለም ። ይህ የሚፈስስ ደም ባይታይም ጦርነት ነው ። ጨዋታ ግን አእምሮን ማፍታታት ነው ። ጨዋታ አካላዊ ሲሆን የተለያዩ ስፖርቶችን ማዘውተር ሊሆን ይችላል ። ጨዋታ አእምሮአዊ ሲሆን አንደበትን በመጠቀም ሰውን እያስደሰቱ ማስተማር ነው ። ጨዋታ መንፈሳዊ ሲሆን ነገረ እግዚአብሔርንና ተፈጥሮን እየተገረሙ ማስተንተን ነው ። በየለቅሶ ቤት አጫዋቾች አሉ ። ለቀስተኛውን በግድ ያስቁታል ። የእነዚህ ሰዎች ዋጋ ትልቅ መሆኑ አይገባንም ። “ጥርስ ባዳ ነው” የሚባለው ሬሳ አስቀምጦ ስለሚስቅ ነው ። ጨዋታ ከሞት በላይ ይሆናል ማለት ነው ።

ጨዋታ ፖለቲካ ካለበት ጥሩ አይደለም ። ምክንያቱም የእኛ አገር ፖለቲካ በአምስት ዓመት አንዴ ሳይሆን የዕለት ኑሮ ሆኗል ። ፖለቲካውም በአሳብ ላይ ሳይሆን በጎሠኝነት ላይ የተመሠረተ ነው ። ስለዚህ ፖለቲካና የዘረኝነት ወሬ ጨዋታን ይጎዳሉ ። በቅርቡ የበቀለ ሕዝብና ጎሣ የለምና ዘመን ያመጣውን ዘረኝነት መጣል ያስፈልጋል ። እሳት የማይታይበት ቃጠሎ ዘረኝነት ነውና ። ሰው ሁሉ እኩል ነውና ሌላውን ጎሣ የሚያሳንስ ቀልድ እንኳን ለመናገር ለመስማት አትፍቀድ ። ጨዋታ መልካም ነው ። ጨዋታ ጨው ነው ፣ ኑሮን ያጣፍጣል ። ጨዋታ የጨዋ ሰው ግብዣ ነው ። “ተገናኝተን ስንጫወት እንደር” ይል ነበር የድሮ ሰው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 21 ቀን 2016 ዓ.ም.
ማስገንዘቢያ

ውድ የዲያቆን አሸናፊ መኰንን መጻሕፍት ወዳጆች መደብራችን የሚገኝበት ሕንፃ ሊፈርስ የተወሰነ ቀን ስለተሰጠን መጻሕፍት የምትገዙ ፈጥናችሁ እንድትገዙ እንጠይቃለን!


ቀጣይ አድራሻችንን ወደፊት እናሳው ቃለን !

0910531997
አራት ኪሎ አርበኞች ሕንፃ ቤርያ መጻሕፍት መደብር

ሰላመ እግዚአብሔር ከሁላችን ጋር ይሁን!
አሁን ገበያ ላይ ያሉት የዲያቆን አሸናፊ መኰንን መጻሕፍትና ዋጋቸው

1- ወዳጄ ሆይ 150 ብር
2- መጻጉዕ 200 ብር
3- የጊዜው ቃል 170 ብር
4- የኑሮ መድኅን 170 ብር
5- እንደ እኔ ከተሰማችሁ 130 ብር
6- ጴጥሮስ ወጳውሎስ 250 ብር
7- የበረሃ ጥላ 160 ብር
8- ኅብስተ ሕይወት 200 ብር
9- የአገልግሎት ቱንቢ 300 ብር
10- ሳምራዊቷ ሴት 200 ብር
11- የሕይወት ውኃ 200 ብር
12- ረጅሙ ፈትል 130 ብር
13- ቅዱስ ጋብቻ 160 ብር
14- የደስታ ቋጠሮ 100 ብር
15- ኒቆዲሞስ 150 ብር
16- አካላዊ ቃል 250 ብር
17- የወዳጅ ድምፅ 130 ብር
18- ተንሥኡ ለጸሎት 60 ብር
19- የሕይወት መክብብ 130 ብር
20- ምዕራፈ ቅዱሳን 150
21- ቃና ዘገሊላ 200
22- የዕለቱ መና 150
23- ኦሪት ዘፍጥረት ትርጓሜ 300
24- እርስ በርሳችሁ 1 20 ብር


20 ፐርሰንት ቅናሽ ይደረጋል፤ ፈጥናችሁ እነዚህን መጻሕፍት ንብረት አድርጉ!
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 23

ማር.5፥ 21-34

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
2024/06/28 22:22:12
Back to Top
HTML Embed Code: