Telegram Group Search
Audio
እግዚአብሔር ይናገራል 2

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (28)

14. ቀጠሮ አክብር

ቀጠሮ የተጀመረው በእግዚአብሔር ነው ። ይህ ዓለም በመለኮታዊ ቀጠሮ የተፈጠረ ዓለም ነው ። ዘመን የሌለው ጌታ ዘመንን ለሰዎች ሰጠ ። ሰው በበደል በወደቀ ጊዜ ለመዳን ቀጠሮ ተሰጠው ። ሰው ከእግዚአብሔር ሳይለይ ከእግዚአብሔር ተለየ ። ለሆዱ እንጀራን ፣ ለአፍንጫው እስትንፋስን የሚያገኘው ከእግዚአብሔር ነው ። እንኳን በምድር በሲኦልም የሚኖረው በእግዚአብሔር ሕይወት ነው ። ጌታችን ወደ ምድር የመጣው ለሰዎች እንጀራ ለመስጠት ሳይሆን ራሱ ኅብስተ ሕይወት መሆኑን ለመግለጥ ነው ። 5500 ዘመን ሰው እንጀራ እየበላ ነበር ። ነፍሱ ግን ስደተኛና ረሀብተኛ ነበረች ። ሰው እግዚአብሔርን የሚክደው ከእግዚአብሔር የተቀበለውን እስትንፋስ መልሶ ሳይሆን በእግዚአብሔር ሕይወት ላይ ቆሞ ነው ። “በማን ላይ ቆመሽ ማንን ታሚያለሽ!” ይባላል ። እርሱ የካዱትን ቢክድ ኖሮ ፍጥረት በምድር ላይ ባልቆየ ነበር ። እግዚአብሔር ቀጠሮን መጀመሩ ብቻ ሳይሆን የሺህ ዘመናት ቀጠሮን የሚሰጥ አምላክ ነው ። የሰው ልጅ በምድር ላይ ከሚኖረው ዕድሜ የረዘመ ቀጠሮ ተሰጠው ። ይህ ብዙ ፍቺ አለው ። የመጀመሪያው የሰው የህልውናው መጨረሻ መቃብር አይደለም ። በሥጋው ያጣውን በነፍሱ ሊክሰው የሚችል አምላክ አለው ። ዛሬ በሥጋ ጉድለታችን ስንፈራ ስንጨነቅ ጌታ ግን አይጨነቅም ። ምክንያቱም በሰማይም ሊጋብዘን ይችላልና።

እኛ ምንም ሳናደርግላቸው የሄዱት ወገኖቻችን የእግር እሳት ሆነውብን ይሆናል ። ደግነታችንን መቃብር ገድቦት ይሆናል ። በሰማያዊው ዓለምም የሚሰጥ አምላክ ግን ሞት ገደቡ አይደለም ። ከሰው ዕድሜ የሚረዝመው ቀጠሮ ለምን ተሰጠ ካልን ከ5500 ዘመን በኋላም የሚኖረው ሰው አዳም ስለሆነ ነው ። ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ከእናንተ ጋር ነኝ ያላቸው እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚኖሩ ሆነው አይደለም ። የእነርሱን ሥራ የሚያስቀጥል ሁሉ ሐዋርያ ስለሆነ በደቀ መዛሙርቶቻችሁ ላይ አድሬ እሠራለሁ ማለቱ ነው ። ስለዚህ ጴጥሮስ ይህን ሲሰማ ብሞትም ሕያው ነኝ ፤ የመንፈስ ልጅ አለኝ ብሎ ይጽናናል ። የአዳምን ቀጠሮ ክርስቶስ ሲሰቀል የነበሩ ሁሉ ፍጻሜውን አይተዋል ። አንድ አዳም ነን ። አንድ ስለሆንን የአዳም በደሉና ጥፋቱ አግኝቶናል ። የአዳም መዳኑና ካሣው ነጻ አውጥቶናል ። በሞት አንድ ሁነን በኑሮ መለያየታችንና መከፋፋታችን ይገርማል ።

የእግዚአብሔርን ቀጠሮ ልዩ የሚያደርገው የማይረሳ አምላክ መሆኑ ነው ። እኛ ቀጠሮአችንን በመርሳት ፣ ባለመመቸት ፣ ባለመፈለግ ፣ በመስጋት ፣ ሌላውን ጉዳይ በማስበለጥ እንሰርዛለን ። እግዚአብሔር ግን መርሳት የሌለበት የሕሊናት ሁሉ ባለቤት ነው ። አይመቸውም አይባልም ፣ እርሱ የሌለውን ና ብሎ መጥራት የሚችል አምላክ ነው ። በሰጠው ተስፋ አይጸጸትምና አልፈልጋችሁም አይለንም ። የሚሽረው የለምና አይሰጋም ። የዘላለም ጉዳዩ እኛ ነንና የእርሱ ውዶች ነን ። እግዚአብሔር ቀጠሮን የሚያከብር አምላክ ነው ። የእርሱ ተከታዮች እርሱን ይመስላሉና ቀጠሮን ያከብራሉ ። “ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ፤” ገላ 4፡4 ።

አንተም ቀጠሮ መስጠትን ልመድ ። ምክንያቱም አንተ እንደ ተመቸህ ያ ሰው አይመቸውምና በድንገት ውረድ ፍረድ አትበል ። ዓመት ሙሉ የረሳኸውን ሰው ዛሬ ስታገኘው አልላቀቅህም ብለህ ስሜታዊ አትሁን ። ቀጠሮ መስጠት ለሰውዬው ምቾት ፣ ለጉዳዩ ክብደት ነው ። ቀጠሮ በሰጠህ ጊዜ ወዳጅህ ተኝቶ እንዲያድር ወይም ተዘጋጅቶ እንዲመጣ ርእሱን ንገረው ። የምፈልግህ በዚህ ምክንያት ነው ብለህ አሳውቀው ። ምናልባት ስጦታ ልትሰጠው ሊሆን ይችላል ። ለምን እንደ ቀጠርከው ካላወቀ ግን የሞት ያህል ያስጨንቀዋል ። ስትቀጥረውም አንተም እርሱም የማትረበሹበት ቦታ ይሁን ። ያ ወዳጅህ የማይፈልገው ሰው ካለ ይዘህበት አትሂድ ። የማይፈልገውና ከዚህ በፊት ተነጋግራችሁበት የተዘጋ ነገርን አታንሣበት ። የቀጠሮውን ርእስ ለመንገር የማይቻል ከሆነ በሻይ ቡና ርእስ አግኘው ። እየጋበዝህ ግን ነገር አታብላው ። በምድር ላይ እጅግ ባለጌ የሆኑ ሰዎች ምግብ እየጋበዙ ነገር አብረው የሚያበሉ ናቸው ። አንድ ኪሎ ሥጋ ጋብዘው አራት ኪሎ ሚጥሚጣ ነስንሰው ይሄዳሉ ።

ቀጠሮ ስትሰጥ ያ ሰው ተጨንቆ እንደሆነ ለማረጋገጥ “ይመችሃል ወይ?” ብለህ ጠይቅ ። ምቾቱን ፍላጎቱን የምትነካበት ሰው እየጠላህ ይመጣል ። ሰው ከምንም በላይ ነጻነቱን የሚወድድ ፍጡር ነው ። ቀጠሮ እጅግ አድርገህ አክብር ። ቀጠሮህን እንዳትረሳ የሚያስታውሱ ማስታወሻዎች አድርግ ። በጸሎት ስፍራህ ወይም በቢሮህ ጠረጴዛ ላይ የቀጠሮህን ወረቀት አስቀምጥ ። ሊያነቃህ የሚችል ደወል ሙላ ። ሴቶች በማስታወስ ጎበዝ ናቸውና አስታውሱኝ ብለህ ንገራቸው ። ቀጠሮ ማክበር የመንፈሳዊነትም የሥልጣኔም መለኪያ ነው ። ምናልባት ያ ሰው ቢያረፍድ ደግሞም ቢቀር ጊዜህን እንዳታባክን የምትሠራውን ሥራ ፣ የምታነበውን መጽሐፍ ይዘህ ውጣ ። ቀረ ብለህ አትቀየም ። ለሰውም አትናገር ። ምናልባት በአደጋ ተሰናክሎ ይሆናል ። ወደ ቀጠሮህ ስትሄድ ጸልይ ። ንግግር ከመጀመራችሁ በፊትም ከዳኅፀ ልሳንና ልቡና እንዲሰውርህ አምላክህን ለምን ። በይበልጥ ለመጨዋወት ቀጠሮ መያዝ መልካም ነው ። አንዳንድ ጉዳዮች በስልክም ሊያልቁ ይችላሉና ለሁሉም ነገር ቀጠሮ ይያዝልኝ አትበል ። ዶሮ በጋን እንዳይሆንብህ ።

ሰው እፈልግሃለሁ ሲልህም አትኩሮት ስጥ ። ምናልባት ላለመኖር እየወሰነ ይሆናል ። ያንተ ቀጠሮ የሰውን ዕድሜ ማስቀጠል ከቻለ ከዚህ በላይ የምትኖርበት ዓላማ የለም ። ዛሬ ቢሞት ለመቅበር ይመችሃል ፣ ተጨንቄአለሁ ሲልህ አይመቸኝም አትበለው ። ያለችው ቀን ይህች ብቻ ልትሆን ትችላለች ። ብቻ ቀጠሮ አክብር ። ክቡርነትህን ማሳያ ነው ። ወላጆችህ ቀጠሮ ይከብዳቸው ነበር ። ሌሊቱን ሙሉ ሳይተኙ ሲንቆራጠጡ ያድሩ ነበር ። የሰውን ዋጋ ስላወቁ ዕድሜ ተሰጣቸው ። ለሰው ክብር የሌለው ዘመኑ አጭር ነው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ግንቦት 26 ቀን 2016 ዓ.ም.
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (29)

ቀጠሮ ያለማክበር ችግር

በዚህ ዓለም ላይ ብዙ ዓይነት ቀጠሮዎች አሉ ። ከወዳጅ ጋር ያለ ቀጠሮ አለ ። በዚህ ቀጠሮ ውስጥ ታማኝ አለመሆን ወዳጅን ሊያሳጣ ይችላል ። ወዳጅን ማጣት በፍቅር ረሀብ መቀጣት ነው ። በቤተ ክርስቲያን ውግዘት የሚባለው ተመክሮ ተዘክሮ እንቢ አልመለስም ያለውን ሰው መለየትና ፍቅር በማጣት እንዲቀጣ ማድረግ ነው ። ፍቅርን ማጣት ወይም ወዳጅን ማሳዘን ራስን እንደ ማውገዝ ነው ። የፍርድ ቤት ቀጠሮ አለ ። የፍርድ ቤት ቀጠሮ የሚያስጠይቅ ፣ በምክንያት የማይቀርበት ነው ። ወደ ፍርድ ቤት በሄድን ጊዜ እንፈራለን ። አንድ ቀን እንደ እኛ ችሎት ፊት የሚቆም ምድራዊ ዳኛ እንዲህ ካስፈራን ሰማያዊው ዳኝነት ብርቱ ነውና ከግፍ መራቅ ይገባናል ። የፍርድ ቤት ቀጠሮ በብዛት ይከበራል ። የሥራ ቀጠሮ አለ ። የሥራ ቀጠሮ አንድ ሠራተኛ የሚመዘንበት የመጀመሪያው መለኪያ ነው ። ለሥራ ቃለ መጠይቅ ቀጠሮ አርፍዶ የሚመጣ ራሱን በራሱ ከዚያ ዕድል ለይቷል ። በአንድ ቀን አቋሙ ቀጣይ ዘመኑን አውቀውታልና ሊቀጥሩት አይፈልጉም ።

ቀጠሮ ስንሰጥ የሰጠነው ቃላችንን ነው ። ቃል የእግዚአብሔር ስም ነው ። የወልድም የኩነት መጠሪያው ነው ። ቃል ብርቱ ነገር ነው ። ቀጠሮ ከመሐላና ከጥብቅ አንቀጽ ጋር የሚወዳደር ነው ። ቀጠሮዎች በተለያየ ምክንያት እንቅፋት ይገጥማቸዋል ። በዚህ ዘመን ላይ ያሉ ወጣቶች የሁሉም ነገር ሥርና ቅርንጫፍ ገንዘብ እየመሰላቸው ይሳሳታሉ ። ወዳጅንም በገንዘብ እንደሚያመጡት ያስባሉ ። በገንዘብ የሚያስቅ ሰው ይገኝ ይሆናል ፣ የሚያስደስት ወዳጅ ግን አይገኝም ። በገንዘብ የሚከብብ ሰው ማግኘት ይቻላል ፣ ውስጥ የሚገባ የልብ ወዳጅ ግን አይገኝም ። ቀጠሮዎች ከሚሰረዙበት ምክንያት አንዱ ገንዘብን ማስበለጥ ወይም ምን አገኛለሁ ብሎ ማሰብ ሊሆን ይችላል ። ፍቅር ግን ምን እሰጣለሁ እንጂ ምን አገኛለሁ ብሎ የሚያሰላ አይደለም ። ደስታ ያለው በመቀበል ሳይሆን በመስጠት ውስጥ ነው ። መርሳት የቀጠሮ እንቅፋት ነው ። መርሳት በዝንጉነት ጠባይ ፣ ብዙ አጀንዳና ወዳጅ በማብዛት ፣ ነሆለል ሰው በመሆን ፣ ሌላ ጊዜም በበሽታ የተነሣ የሚከሰት ነው ። መርሳትን ግን በጽሑፍና በደወል ማሸነፍ ይቻላል ። እየመረጥን የምንረሳ ከሆነም የእኛ ችግር ነው ። መርሳት ብዙ ጭንቀትና ውጥረት በማብዛት የሚመጣ በመሆኑ እኔ እኮ እረሳለሁ ብሎ የሚታለፍ አይደለም ። ያለ ዕድሜ የሆነ እንደሆነ ምንድነው ችግሬ ብሎ መጠየቅና መልሱን መፈለግ ያሻል ። አለማንበብ የመርሳትን ችግር ያመጣል ። ከሰዎች ጋር አለመገናኘትና አለማውራት መርሳትን ይወልዳል ።

ወዳጅን ቀጥሮ ማናገር ራስን የማከምና የመፈወስ ትልቅ ዘዴ ነው ። ብዙ ውጥረቶች ይቀላሉ ። የመኖር ፍላጎት እየጨመረ ይመጣል ። ያለንን ነገር በደስታ መጠቀም ይቻላል ። ተቀጣጥሮ ስልክ መዝጋት ይህ የጠባይ ዝቅታ ውጤት ነው ። ይህን የሚያደርጉ አገልጋይ ነን የሚሉም አሉ ። እንዲህ የኮሩበት አገልግሎት አንድ ቀን እየፈለጉም አያገኙትም ። አገልግሎትም ጡር አለው ። ሁልጊዜ ሊመቸን አይችልምና አስቀድመን ማሳወቅ ይገባናል ። ሰውን ከሰው አወዳድረን መቅረት ግን ነውር ነው ። የሁሉም ሰው ክብሩ እግዚአብሔር ነው ። ስለዚህ ሰው ሁሉ እኩል ነው ። አስድመን የሰጠነውን ቀጠሮ ማክበር ይገባል ። አንዳንድ ሰዎችን ተቀይመናቸዋል ወይም እነርሱን ማግኘት እየጎዳን ተቸግረን ይሆናል ። ይህንን በግልጥ ነግረን ማረም ወይም ቀጠሮ አለመያዝ ተገቢ ነው ። ሰው ለሰላሙ ዋጋ መክፈል አለበት ። ሰላማችንን ሠውተን የምናደርገው ግንኙነት ውስጣችንን እየጨረሰው ይመጣል ። ደግሞም የሚያኖረን እግዚአብሔር ነውና የሚያውኩንን የተቀየምናቸውን ሰዎች በግልጽ መንገርና መፍታት አስፈላጊ ነው ።

ቀጠሮአችንን ለማሳካት አለመቻላችንን መንገር ክብረት ነው ። እንዲሁ መቅረት ግን ያ ሰው ለእኛ ያለውን አመለካከት ዝቅ እንዲያደርግ ያስገድደዋል ። በመጀመሪያ ይበሳጭብናል ፣ ቀጥሎ ለእኛ ያሰበውን ትልልቅ ነገሮች መሰረዝ ይጀምራል ። ማንም ሰው ዋጋ የሚከፍለው ለአክባሪው ነው ። ሰዎች ቀጥረውን ቢቀሩ አንዳንድ ጊዜ ለበጎ ሊሆን ይችላል ። ሰብቅ ይዘውብን እየመጡ ከሆነ ለቀጣይ አንድ ዓመት ሰላማችንን ሊሰርቁት ነውና ቢቀሩ ይሻላል ። ወረኞችን አሉህና አሉሽ ማለት የሚወዱትን አለመቅጠርና አለማግኘት መልካም ነው ። ወሬውን እስኪነግሩን እንቅልፍ የላቸውም ፣ እኛ ሰምተን እንቅልፍ ስናጣ ግን ያን ጊዜ ይተኛሉ ። አምልኮተ እግዚአብሔርና ቃለ እግዚአብሔር በምንሰማበት ሰዓት ቀጠሮ መያዝ ክልክል ነው ። ካልሞትን በቀር ቤተ ክርስቲያን መቅረት የለብንም ። ስንሞትም የምንቀበረው እዚያው ነው ። በቀጠሮአችን ሰዓት ወዳጅነታችን እንዲቀጥል የማንስማማባቸውን ርእሶች መተው ይገባናል ። ክርክር አንዳንድ ጊዜ እኔ የበላይ ልሁን የሚያሰኝ የሥጋ ሥራ ነውና ፍቅርን ይጎዳል ። ቀጠሮን የሚጎዳው ሌላው ነገር ማርፈድ ነው ። አንዳንድ ማርፈድ የመቅረት ያህል ነው ። የአበሻ ቀጠሮ የሚባል የለም ። ቀጠሮ ፣ ቀጠሮ ነው ። ማርፈድን መዘናጋት ፣ መተኛት ፣ ጊዜን መለካት አለመቻል ፣ ወቅቱን አለማገናዘብ የሚወልደው ነው ። ማርፈድ ተጨማሪ ወጪ ነው ። አርፍደው አውሮፕላን ያመለጣቸው ተጨማሪ ወጪ ያወጣሉ ። ጓደኛቸው ተበሳጭቶባቸው የሄደባቸው ተጨማሪ ይቅርታና ማሳመን ያስፈልጋቸዋል ። ማርፈድ ጠባዩ ነው መባል ሞት ነው ። ሙሽሮች በሰዓቱ መድረስ የጠሩትን ሰው ማክበር ነው ። እስከማውቀው ድረስ ምግብ እያዩ ሙሽራን መጠበቅ የአገራችን ባሕል አይደለም ። እየበሉ እየጠጡ መጠበቅ ተገቢ ነው ። በሰርጉ ቀን ያረፈደ ፣ ትዳሩም ላይ ብዙ ማርፈድ ይገጥመዋል ።

ሰውን ማክበር ለራሳችን ያለን ክብር ውጤት ነው ። ቀጠሮ ማክበር ራስን ማክበር ነው ። ያደጉ አገሮች ሁሉ ያደጉት ቀጠሮን ወይም ሰዓትን በማክበር ነው ። ሰዓት ዋጋ ያጣው እኛ አገር ነው ። ማደግ ፈልገን በሰዓት ቀልደን አይሆንም ። ባለጉዳይ የቀደመው ሠራተኛ ማፈር አለበት ። አገር በዘፈን ሳይሆን በመሥዋዕትነት ታድጋለች ። ሌላ አገር ያለን ይመስል አንዷን አገራችንን ማጎሳቆል ሊበቃ ይገባዋል ።


ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 6 ቀን 2016 ዓ.ም.
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (30)

15. የሰውን ነጻነት አክብር

አንዳንድ ገዥዎች ተነሥተው ነጻነት ሰጠናችሁ ይላሉ ። ሰው ለሰው ነጻነት መስጠት አይችልም ። የሰው ልጅ በተፈጥሮው ነጻነት ያለው ፍጡር ነው ። ደጋግ ነገሥታት ይህን ነጻነት ያከብሩ ፣ ያስመልሱ ይሆናል እንጂ ሊሰጡ አይችሉም ። የነጻነታችን ጌታ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ነጻነት ነጻ መሆን እንደ ልብ መፋነን አይደለም ። ነጻነት የሥጋን ፣ የነፍስን ፣ የመንፈስን መንሰራፋት ማክበር ነው ። ሰው ወደ ወደደው አገርና ግዛት ሂዶ መኖር ፣ መንቀሳቀስና መነገድ ፣ ማተረፍና መውለድ ይችላል ። ይህ የሥጋ ነጻነት ነው ። የነፍስ ነጻነቱ የማሰብ ፣ የመናገርና የመኖር መብት ነው ። የመንፈስ ነጻነቱ የወደደውን አምላክ የማመን ፣ የማምለክና የመደሰት ልዕልና ነው ። ነገሥታት ይህን ነጻነት በበላይነት መጠበቅና ማስጠበቅ ይገባቸዋል ። እኔ እንደማስበው አስብ ማለት ሳይሆን ወደ እኛ አሳብ ሰዎችን በፍቅርና በአመክንዮ መሳብ እርሱ ነጻነትን ማክበር ነው ። እኛ እንደምናምነው የማያምን ሰውን ላጥፋህ ልደምስስህ ማለት ከእግዚአብሔር ጋር መጣላት ነው ። ይህች ዓለም የሰዎችም የእንስሳትም ዓለም ናት ። የጋራ ዓለም ናትና በጋራ ጉዳይ አንድ እየሆንን የሌላውን የግል መብት ማክበር አለብን ።

ስለ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ብዙ ሰምተናል ፣ ብዙ ተናግረናል ። ዲሞክራሲ ባለመምጣቱም ኀዘን ገብቶናል ። የምንመኘውና ለዘመናት አትመጣም ወይ  ብለን የምንጣራው ዲሞክራሲ የሌላውን መብት ማክበር ነው ። የራስን ግዴታ አውቆ የሌላውን ድንበር አለመዳፈር እርሱ ዲሞክራሲ ነው ። የሰዎችን የማመን ፣ የመናገርና የመኖር መብት ማክበር እርሱ ዲሞክራሲ ይባላል ። ዲሞክራሲ እንደ ምርት ከውጭ አገር ተጭኖ የሚመጣ አይደለም ። ዲሞክራሲ በመካከላችን ያለ ከራስ ወዳድነት ወጥተን ስለሌሎች በማሰብ ተግባራዊ የምናደርገው ነው ። ለራሳችንና ለወገናችን የነፈግነውን ዲሞክራሲ ማንም ሊሰጠን አይችልም ። ሁልጊዜ ተሸማቀን ከመኖር አንድ ጊዜ ተስማምተን ነጻነትን ማስፈን ይገባናል ። በኑሮአችን ውስጥ ሁሉም ሰው የራሱን ነጻነት ማስከበር ይፈልጋል ። ዲሞክራሲ ግን የሌላውን ነጻነት ማክበር ነው ። ዲሞክራሲን ለማስፈን ሰው ከራሱ ውጭ የሚታገለው ነገር የለም ። የነጻነታችን ትልቁ ጠላት እኛው ነን ።

ሰዎች የተለያየ ፖለቲካዊ አመለካከት ይኖራቸዋል ። እንደ እኔ አስቡ ብሎ መጫን ግን አትኑሩ ብሎ መፍረድ ነው ። እንጨትና እንጨት ሲፋተግ እሳት ይወጣዋል ። የሰዎችም መነጋገርና መከራከር እውቀትን ይፈነጥቃል ። አንድነት ማለት አንድ ዓይነት መሆን አይደለም ። የተለያየን መሆናችን ውበትን እንጂ ጭንቀትን የሚፈጥር አይደለም ። ሰዎች የራሳቸው ሃይማኖት አላቸው ። ከምናምነው ተቃራኒ ነገር ቢያምኑም የመኖር መብት አላቸው ። በምንም መንገድ አገር የዜጎች እንጂ የአንድ ሃይማኖት መሆን የለባትም ። ይህ የዜጎችን መከራ ያበዛል ። የነገሥታትም ድርሻ ሃይማኖትን ማስፋፋት ሳይሆን ሰላምና ዕድገትን ማስከበር ነው ። ሰዎች በመሰላቸው መንገድ ራሳቸውን በተለያየ ሱስ እየጎዱ ሊሆን ይችላል ። መጥላትና ማሳደድ ግን አንችልም ። ወደ ቀናው መንገድ በፍቅር መመለስ እንችላለን ። በምድር ላይ ለሃይማኖት ሰው የተሰጠው ትልቅ መሣሪያ ፍቅር ብቻ ነው ።

አንተ ግን የሌላውን ነጻነት አክብር ። ፍላጎታቸውን ተጭነህ ወዳጆችህ የምታደርጋቸው የሉም ። ለጊዜው ያደፍጡ ይሆናል ፣ አቅም ሲያገኙ ግን ጥለውህ ይሄዳሉ ። ሰዎች የራሳቸው የሆነ ጊዜ ሊፈልጉ ይችላሉ ። ለፍላጎታቸው ተዋቸው ። ዛሬ አንተን ማግኘት አይፈልጉ ይሆናል ። ከራሳቸው ችግር ጋር እየታገሉ እንጂ አንተ ርካሽ ሰው ስለሆንህ አይደለም ። ሁለት ጊዜ ያህል ደውለህ መልስ ካልሰጡህ ተዋቸው ። ስላልፈለጉህ በማትፈለግበት ቦታ ጊዜ አታጥፋ ። አንተን የሚፈልጉህ “በመጣልኝ” ብለው የሚሳሱልህ ብዙ አሉ ። ሰው የሚጠሉትን ሲያሳድድ ፣ የሚወዱትን ይከስራል ። ራስህን ዝቅ ማድረግ ተገቢ ነው ። ራስህን ርካሽ ማድረግ ግን እንድትጣል ያደርግሃል ። በመገኘትህ የምትጠቅማቸው ሰዎች ይኖራሉ ፣ መገኘትህንና ቅርበትህን ካቃለሉ ግን ራቃቸው ። ክብር በሌለበት ፍቅር የለም ፣ ፍቅር በሌለበትም እግዚአብሔር የለም ። ማንንም ሰው አሳምን እንጂ አትለማመጥ ። የሰውነት ክፍሎችህ ካንተ ጋር ናቸው ። በሰው እጅ አትጎርስም ፣ በሰው ትንፋሽ አትኖርም ። የራስህን ሕይወት የሰጠህን ጌታ አክብር ።

ሰዎች የሚወድዱት አለባበስ ፣ የኑሮ ዘይቤ ፣ የቤት አሠራር ፣ የትዳር ምሪት ፣ የልጆች አስተዳደግ አላቸው ። ቋሚውን እውነት አሳውቃቸው እንጂ በእኔ መንገድ ካልሄዳችሁ እያልህ አትጎትታቸው ። የጣሉህ ሰዎች የጎተትካቸው እንቢተኞች ናቸው ። እገሌ ይጾማል አይጾምም ፣ እገሌ በቅድስና ነው ያለው በርኵሰት እያለህ በሰው ጓዳ አትዋል ። ይህ ርካሽነት ነው ። የራስህን ኑሮ ኑር ። ካንተ የሚፈልጉ ከሆነ እንኳን በወዳጆችህ በጠላትህም አትጨክን ። እንኳን አንተን ሰጪ አደረገህ ። የማይፈልጉ ሰዎችን ካልመከርኩ አትበል ። እርዳታህን የሚሸሹ ሰዎችን በግድ ካልረዳሁ አትበል ። የከበረውን ነገር ዋጋ በማይሰጡ ሰዎች ፊት አትጣል ። ውድ ጊዜህንም ተራ ነገርን ከሚፈልጉ ሰዎች ጋር አታባክን ። በማትፈለግበት ቦታ አትገኝ ። ምንም ነገር ስታደርግ ሰዎችን አስፈቅድ ። ያለ ፈቃዳቸው የምታደርገው ነገር ላንተም ለእነርሱም ደስታ አይሰጥም ። በጣም ጥንቃቄም ለስህተት ይዳርጋልና እጅግም ጠንቃቃ ፣ እጅግም ጻድቅ አትሁን ። ወደ ጓደኛህ ቤት እግር አታብዛ ። ወዳንተ ቤት እግር ቢያበዙ ግን ክርስቶስን እንደምትቀበል አድርገህ ተቀበላቸው ። የልብህን ሁሉ ፣ ለሁሉ አትናገር ። ሰዎችም ሁሉን እንዲነግሩህ አትፈልግ ። ባለትዳሮች ካልጋበዙህ በቀር ልዳኛችሁ አትበል ። ባልዬው በሌለበት ቤት ሚስቲቱ ብትቀጥርህ አትሂድ ።

በአገራችን በሰው ገላም ካላዘዝን የምንል ደፋሮች ነን ። የምንኖረውም በመጠባበቅ እንጂ ያመንበትን አይደለም ። በገዛ ሕይወታችን ላይ ድራማ የምንሠራ ምስኪኖች ነን ። ማኅበራዊነታችን መልካም ነው ። የሌላውን መብት መጋፋት ግን ነውር ነው ። በሁሉም ነገር ላይ አስተያየት መስጠት ግዴታችን ይመስለናል ። ለሁሉም መልስ አይሰጥም ። ብቻ የሰዎችን ነጻነት አክብር። ሊሄዱ የሚፈልጉትን በሰላም ሸኝ ። የሚመጡትን ደጎች ተቀበል ። በትዝታ ታስረህ የዛሬን ኑሮ አትሰርዝ ። ጨርሻለሁ ብለው መሄድ የማያውቁ ሰዎችን አጨራረሱን አሳያቸው እንጂ እንዲያውኩህ አትፍቀድላቸው ። ምክንያቱም ያንተ ኑሮ ይህ ነው ፣ እነርሱ ግን አማራጭ አላቸውና ። ርቀውህ የነበሩ ሰዎች እንደገና ሲመጡ በጥንቃቄ ተቀበል ። ምናልባት ያልጨረሱትን ተንኮል ለመጨረስ ይሆናል ። መጠንቀቅ ይቅር አለማለት አይደለምና ። ዕድሜህ እንዳያጥር ለአልምጦች ጋር አትኑር ! ከራስህ ጋር መሆን ጣፋጭ ነው ፣ ሰዎች ካልመጡ ሕይወትህ የተሰረዘ አይምሰልህ ! ሁልጊዜ ሰዎች አይገኙምና ከራስህ ጋር ልታደርግ የሚገባውን ዛሬውኑ አቅድ ! የምትፈልገውን በትክክል እወቅ ፤ ሕይወትህ መደሰት ትጀምራለች!

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 7 ቀን 2016 ዓ.ም.
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 21

ማር.4፥ 21 - 41

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 21

ማር.4፥ 21 - 41

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
እግዚአብሔር ይናገራል 3

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
እግዚአብሔር ይናገራል 3

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (31)

16. ዜማ

ዜማ በሰው ነፍስ ውስጥ የተቀመጠ ጥልቅ ፍላጎት ነው ። ዜማ ምድራዊውን ሰው ሰማያዊ የሚያደርግ ነው ። የነፍስ ሀልዎት መገለጫ ነው ። ነፍስ ስትታደስ ሥጋም አብሮ እንደሚታደስ ዜማ ይነግረናል ። ዜማ ሰዎችና እንስሳት የሚካፈሉት የጋራ ፍላጎት ነው ። ዜማ ሲሰሙ አደገኛ የሚባሉ አራዊት ይመሰጣሉ ። ዜማ ጨካኙን የማራራት አቅም አለው ። ቀሳውስት ቸገረኝ እንጂ ጨነቀኝ ሲሉ አይሰማም ። ጭንቀትም በጉልህ አይታይባቸውም ። የዚህ ምሥጢሩ ዜማ ነው ። ዜማ ያድሳል ። የከበደንን ደመና ያነሣል ። ዜማ ደስታን ፣ የአእምሮ መፍታታትን ፣ ጣዕምን ፣ ተደማጭነትን ፣ ተወዳጅነትን ያጎናጽፋል ። በዜማ ውስጥ ብዙ መልእክቶች አሉ ። ዜማ ምስጋናንና ትምህርትን በጣዕም ለማስተላለፍ የሚረዳ ነው ። ዜማ የታላቅ ፍልስፍና መገለጫ ነው ። ዜማ በሰማይ የሚጠብቀን ድግስ ነው ። ቅዱስ ያሬድ የዜማው ባላባት እስከ ዛሬ ድረስ ተሰምተው የማይጠገቡ ዜማዎችን ለቤተ ክርስቲያን አበርክቷል ። በርግጥ መንፈሳውያን እንደ መሆናችን እግዚአብሔር እንደ ገለጠለት እናምናለን ፤ የስጦታውን ምንጭም አንስትም ። ቅዱስ ያሬድ እንዲህ ተቀብሮ መቅረቱ ኢትዮጵያዊ መሆኑ ነው ። የሌላው ዓለም ሀብት ቢሆን ኖሮ የየቀኑ ርእስ ይሆን ነበር ።

ዜማ የትልቅ ሥልጣኔ መገለጫ ነው ። ዜማን በኖታ ዓለም ከማቅረቡ በፊት ቅዱስ ያሬድ አዘጋጅቶታል ። ዜማ ቋንቋ ነው ። ስብሐተ እግዚአብሔር የሚደርስበት ሰረገላ ነው ። ዜማ ክንፍ ነው ፣ ወደ ሰማየ ሰማያት የምንወጣበት ነው ። ጸሎታችንን በዜማ ብናደርስ የምንጸልየውን እናስተውለዋለን ፣ እንባ በዓይናችን ይሞላል ፣ ልባችን በመለኮት ፍቅር መቅለጥ ይጀምራል ። ጮክ ብለን ማዜምና መዘመር በጣም ወሳኝ ነው ። በሳምንት አንድ ቀን እንኳ አፍ አውጥተን ብናዜም የከበደን ነገር ይቀለናል ። ዜማ የነፍስ ምግብ ፣ የጭንቀት ዱላ ነው ። ማንጎራጎር የሚወድዱ ሰዎች ደስተኞች ናቸው ። እያንጎራጎሩ ሲያለቅሱ ይታደሳሉ ። እንባ ወደ ውጭ ካልፈሰሰ ወደ ውስጥ ይፈሳል ። ያን ጊዜ ሰባራ ሰው ያደርገናል ። ዜማ ስብሐተ እግዚአብሔር የሚቀርብበት መሠዊያ ነው ። እግዚአብሔርን የሚማርከው ዜማው ሳይሆን የልባችን መቃጠል ነው ። ዜማ ግን ምድራዊነታችንን ሰማያዊ ያደርገዋል ።

የሚያዜሙ ሰዎች ብዙ ጊዜ እውቀት አይወድዱም ። በዚህ ምክንያት “ድምፅና ቁንጫ ባዶ ቤት ይወዳል” እየተባሉ ይተቻሉ ። የሚያዜም ሰው ግጥም ፣ ቅኔ ፣ የንግግር ችሎታን ማዳበር አለበት ። በርግጥ የሊቃውንቱን ቅኔ ለዓለም የሚያደርሱት ዜመኞች ናቸው ። የሚያዜሙም ከእውቀት መራቅ አይገባቸውም ። ዜማ ሙያ ሲሆን ለጥቂቶች ነው ። አምልኮ ሲሆን ግን ለሰው ልጆች ሁሉ ነው ። አእዋፋት በማለዳ ያዜማሉ ። ባናያቸውም እንወዳቸዋለን ፣ ዜማ እንደሚያነቃም እንረዳለን ። የሚያዜሙ ሰዎች በሰው ነፍስ ውስጥ አሉ ። ሰው ከውጫዊ አካሉ ይልቅ ነፍሱ ስፋት እንዳላት ዜማና ተጽእኖው ይገልጥልናል ። ዜማ የተለያየ መልእክት አለው ብለናል ። የማኅበረሰብ መግባቢያ ቋንቋ ነው ። ሰርግን ፣ ጦርነትን ፣ ደስታን ፣ ኀዘንን በዜማ እንወጣለን ። ሥርዓት ያላቸው ዜማዎች ፣ የማኅበረሰቡ ግኝት የሆኑ ግጥሞች ለሰርግ መዋል አለባቸው ። ዜማ የዝሙት ማስታወቂያ ሲሆንና እጅና እግርን ማወደሻ ሁኖ ሲቀር ይተቻል ። መንፈሳዊነት ማኅበረሰብን የሚደፈጥጥ አይደለም ። በሰርጌ ጌታ ይክበር የሚሉ አሉ ፣ ጥሩ ነው ። ጌታ ግን የሚከብረው በሁለት ሰዓት ፕሮግራም ብቻ ሳይሆን በኑሮ ውስጥ ነው ። ሚስትህን በአጋፔ ፍቅር ስትወዳት ፣ ባልሽን እንደ ራስ ስታከብሪው ያን ጊዜ እግዚአብሔር ይከብራል ።

በዜማ መለቀስ ፣ ኀዘን መተንፈስ አለበት ። ያልወጡ ኀዘኖች ብዙዎችን ለድባቴ እየዳረጉ ይገኛሉ ። አገራችን ታላላቅ ሰዎች የነበሩባትና ያሉባት አገር ናትና ደስታንም ኀዘንንም መግለጫ አበጅተዋል ። ደግሞም የባሕላችን ማሳያ ነውና ሊከበር ይገባዋል ። አለማልቀስ ዘመናዊነትም መንፈሳዊነትም አይደለም ። ሬሳ አስቀምጦ አላለቅስም ማለት ጉራ ሲሆን አብረው የሚያላቅሱ ሲሄዱ ውጋቱ ይጀምራቸዋል ። እንዴት ሰው ሞትን እያስተናገደ ለማልቀስ ይሳሳል ?

አገርን የሚያወድሱ ፣ ጀግንነትን የሚያነሣሡ ዜማዎች አንድን ትውልድ የአገር ዘብ አድርጎ የማቆም አቅም አላቸው ። እዚህ የምንጽፈውና የምናመልከው በዳር ድንበር የሚጠብቅ ወታደር ስላለ መሆኑን ማወቅና ክብር መስጠት ይገባናል ። ከዜማ ጋር የዜማ መሣሪያዎችን መለማመድ ግድ ይላል ። ቢያንስ አንድ የዜማ መሣሪያ ማወቅ ለቀጣዩ ዕድሜ ፣ ለእርጅና ብቸኝነት ወሳኝ ነው ። ዜማ ለማኞች እንኳ ጨካኙን የሚያራሩበት ነው ። የዜማ ዕቃ ይዘው የሚያዜሙም ከመንገዳችን ቆም ያደርጉናል ። ዘወትር ከጸሎታችን ጋር ድምፅ አውጥተን ብንዘምር ላሉብን ውጥረቶች ቅለት ይሰጠናል ። ነገር ግን አጠገባችን ያለውን ሰው እንዳንረብሽ ፣ ተወዳጁን አምላክ በእኛ ረባሽነት እንዳናስጠላው መጠንቀቅ ያስፈልጋል ። ዜማ የራሱ ሥርዓት አለውና ሊጠና ፣ ሊያድግና ሊበረታታ ይገባዋል ። ከሕይወት ሥነ ሥርዓት አንዱ ዜማ ማዜም ነው ። በቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት የዜማ ዕቃ ጸናጽል ፣ መቋሚያና ከበሮ ነው ። የምእመናን የዜማ ዕቃ በገና ፣ መሰንቆ ፣ ክራር ፣ እንዚራ ተጠቃሽ ናቸው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 10 ቀን 2016 ዓ.ም.
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (32)

17. ማኅበራዊ ኑሮ ይኑርህ

አንድነትን በሚመለከት አራት ዓይነት ኅብረቶች አሉ ። የመጀመሪያው ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ያለው አንድነት ነው ። ሁለተኛው ሰው ከራሱ ጋር ያለው አንድነት ነው ። ሦስተኛው ሰው ከሰው ጋር ያለው አንድነት ነው ። አራተኛው ሰው ከአማኝ ጋር ያለው አንድነት ነው ። ከእግዚአብሔር ጋር ያለን አንድነት እርሱን በማወቅ ፣ በማምለክና ትእዛዛቱን በመፈጸም ፣ በንስሐ በመታደስ ላይ የተመሠረተ እንዲሁም የሚቀጥል ነው ። ሰው ከራሱ ጋር ያለው አንድነት ከእግዚአብሔር ጋር ባለው አንድነት ላይ የሚመሠረት ነው ። ሰው ከራሱ ጋር መለያየት ካመጣ ፣ ውስጣዊ ግጭት ካለበት ሰላምና ደስታ እንዲሁም የመኖር ፍላጎት እየራቀው ይመጣል ። ሰው ከሰው ጋር ያለው አንድነት ከራሱ ጋር ባለው አንድነት መሠረት ላይ የሚቆም ነው ። ከራሱ ጋር አንድ ያልሆነ ከሌላው ጋር አንድ ሊሆን አይችልም ። ሰው በማመን እርሱን ከሚመስሉት ጋር አንድ የሚሆንበት ዘላቂ አንድነት አለ ። ይህን አንድነት ልዩ የሚያደርገው በሰማይም የሚቀጥል በመሆኑ ነው ።

አማኒ የሆነው ወንድማችን ዘመዳችን ፣ ጎረቤታችን ፣ የቅርብ አገልጋያችን ላይሆን ይችላል ። ያለን ግንኙነት መንፈሳዊ ነው ። ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም እንድንኖር መጽሐፍ ያዝዘናል (ሮሜ. 12፡18)። አንዳንዴ አዳጋች ይሆናልና ቢቻላችሁስ የሚል ሚዛን ያስቀምጧል ። ከተቻለን ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም መኖር መልካም ነው ። ሰዎች ግን የእኛ እምነትና ህልውና እየረበሻቸው ሊጣሉን ይችላሉ ። ክርስቲያን በምንም መንገድ ሌላውን የሚያውክ ሊሆን አይችልም ። እርስ በርሳቸው የዘረኝነት ችግር ቢኖርባቸውም ጌታችን ግን ከአይሁድ ወገን ተወልዶ የሳምራውያን ወዳጅ ነበረ ። ሰው ያገለላቸውን ቀራጮችና አመንዝሮች ከእርሱ ጋር አብረው እንዲበሉ ይጋብዛቸው ነበር ። ክርስቲያን ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር መስፈርት የሚያደርገው ሃይማኖቱን ወይም እንደ እኔ ካላመኑ የሚለውን አመለካከት አይደለም ። ክርስቲያን በመጽሐፍ እንጂ በሰይፍ የሚያሳምን አይደለምና ።

ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር መዋሸት አለብን ማለት አይደለም ። ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር የራሳችንን አመለካከትና ሃይማኖት እያከበርን የሌሎችንም ማክበር ነው ። የሃይማኖትህ መሪ የሆነው አባት ከቡዲስት ወይም ከአረሚ ጋር ሰላም ሲባባል ስታይ የምትበሳጭ ከሆነ ይህችን ዓለም ያንተ እምነት አባላት ብቻ እንዲኖሩባት እየፈለግህ ነው ። የራስን ይዞ የሌላውን ማክበር ይቻላል ። ሰዎች ያመኑበትን በጥላቻ ለማስጣል ስንሞክር የበለጠ እንዲያከሩ እናደርጋቸዋለን ። ምንም ውክልና የሌላቸው ለቤተ ክርስቲያን መልስ እንሰጥላታለን የሚሉ ወጣቶች በየጊዜው በሃይማኖት ስም ጥላቻን ሲዘሩ ይታያሉ ። እዚህ ያለውን አይሁድ ስትነካው ኢየሩሳሌም ያለው ክርስቲያን መኖሪያ ያጣል ። ሁሉም አገር አለውና ። እዚህ ያለውን ሙስሊም ስትነካው ግብጽ ያለው ክርስቲያን መሸበር ይጀምራል ። የዚህች ዓለም ሰላም የቆመው በሰው ልጆች ሁሉ ነጻነት ላይ ነው ። የራሱ እምነት ያሳረፈው ሰው የሌላውን በመንቀፍ ጊዜውን አይፈጅም ።

ማኅበራዊ ኑሮ በመከባበር ላይ የተመሠረተ ነው ። ማኅበራዊ ኑሮ በብዙ መንገዶች ሊጎዳ ይችላል ። የብቸኝነትና የጭንቀት መንፈስ ሲታገለን ማኅበራዊ ኑሮአችን እየተጎዳ ይመጣል ። መሸሽን ገለል ብሎ መቀመጥን እንወዳለን ። አንዳንድ ጊዜም ከትዳራችንና ከልጆቻችን መሸሽ ይታየናል ። የብዙ ትዳር ችግር ማንም ያላወቀው ጭንቀት ነው ። መነጫነጩ ፣ ስካሩ ውጤት ነው ። መነሻው ግን ጭንቀት ነው ። ሥሩን ካልፈወስን ቅርንጫፉ አይድንም ። ስለ ሰዎች ያለን ተገቢ ያልሆነ አመለካከት ይኖራል ። ይህ ከቤተሰብ ፣ ከአስተዳደግና ከደረሰብን ጉዳት የተነሣ የሚመጣ ነው ። በዚህ ምክንያት ከማኅበራዊ ኑሮ እንርቃለን ። ልጆች ሲያድጉ ከሰው ጋር እንዲቀላቀሉ ፣ ሰርግም ልቅሶም እንዲያዩ ተደርገው ሊሆን ይገባል ። ዛሬ ብንሸፍናቸው ነገ ብቻቸውን ይጋፈጡታል ። ልጆችን ተክቶ የሚኖር ወላጅ ሞቱን የረሳ ወላጅ ነው ። ዘመናዊነት ማኅበራዊነትን እየናደ ነው ። የትዳር ክፍተቶች ፣ የፍቺ መበራከቶች ማኅበራዊነትን ይጎዳሉ ። የሚሰሙና የሚታዩ ዘግናኝ ወንጀሎች ሰውን ፈሪ በማድረግ እንዲራራቅ ያደርጉታል ። ወንድ ልጃቸውን ለሴትም ለወንድም አደራ ብለው ለመሄድ የተቸገሩ ወላጆች አሉ ። የሚሰሙት ነገር ሕሊናቸውን አርክሶታል ፣ ልባቸውን ፈሪ አድርጎታል ። የገዛ ሴት ልጃቸውን ለአባት ትተው መሄድ የሚፈተኑ እናቶችን እናውቃለን ። ማኅበራዊነት በአባትና በልጅ መካከል ከፈረሰ ሌላ ቦታ መጠበቅ ከባድ ነው ።

ዘመናዊው ዓለም የግል የሆኑ ነገሮችን በማብዛት አንድነትን የማፍረስ ዘመቻ ላይ ነው ። በየጊዜው በላቦራቶሪ ተመርተው በሚለቀቁ በሽታዎች ሰው ሰውን እንዳይቀርብ ሰይጣናዊ ተልእኮአቸውን እየተወጡ ነው ። በዚህ ምክንያት የሰው ልጅ በብቸኝነት ዕድሜው እያጠረ ይመጣል ። ማኅበራዊነት ዕድሜን ይቀጥላል ፣ ደስታንም ይሰጣል ። አብረው ካልበሉ ፣ አብረው ካልተደሰቱ ፣ አብረው ካላለቀሱ የዚህ ዓለም ኑሮ ሊገፋ አይችልም ። ራስ ወዳድነትና ስስት ፣ ሁሉንም ነገር ስሌት ውስጥ ማስገባት የማኅበራዊነት ጠላት ነው ። ለሌሎች ስንኖር ሌሎች ለእኛ ይሞቱልናል ። የምናጭደው ከዘራነው በላይ ነውና ። ደግሞም ውጤቱን በማሰብ ሳይሆን በራሱ ትልቅ ደስታ በመሆኑ ማኅበራዊነት ሊጠነክር ይገባዋል ። አንተም ማኅበራዊነት አስፈላጊህ ነውና የሠራኸውን የግል ደሴት አፍርሰህ ከሰው ተቀላቀል ! ሞኝ አትሁን ከምትሰጣቸው የሚሰጡህ ይበልጣል ! ፌስ ቡክ ላይ ልቅሶ መድረስ ፣ ቲክ ቶክ ላይ ሙሾ ማውረድ ቁምነገር አይምሰልህ ፣ የቀኑ የወሬ ጥማትህ ማሟያ ወይም ምን ላውራ ለሚለው ጭንቀትህ ማረፊያ ነው ! ማኅበራዊነት አካላዊነት ነው ! መሄድ ፣ ጊዜ መስጠት ፣ አቅፎ ማጽናናት ፣ በጎደለው መሙላት ነው !


ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 14 ቀን 2016 ዓ.ም.
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 22

ማር.5፥ 1 - 20

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 22

ማር.5፥ 1 - 20

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
እግዚአብሔር ይናገራል 4

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
እግዚአብሔር ይናገራል 4

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (33)

18. ስፖርት

ከሕይወት ሥነ ሥርዓቶች አንዱ ስፖርት ማዘውተር ነው ። ለታላቁ ሩጫ በዓመት አንድ ጊዜ መሮጥ ፣ ለፎቶ እንጂ ለጤና ምንም ጥቅም የለውም ። የሰውነት እንቅስቃሴ ዕለታዊ ግዳጅ ነው ። እጅ ለመሥራት ፣ እግር ለመራመድ እስከ ተሠራ ድረስ መሥራትና መንቀሳቀስ አስፈላጊ ነው ። አሊያ የሞት ጎረቤት ፣ የበሽታ ዳስ ሆኖ መኖር ነው ። “መቀመጥ ቆመጥ ነው” እንዲሉ ። ዘመናዊነት ከጎዳን ነገር አንዱ የስንፍና ሠራዊት ማብዛቱ ነው ። ከምግብ እንኳ የሚታኘክ አንፈልግም ። በፋብሪካ ተቀነባብሮ ፣ ልሞ ፣ በሚሳብ መልክ መውሰድ ነው ። ይህ ጥርስ ያላወጡ ፣ ምግብ ያለመዱ ሕፃናት ይወስዱት የነበረ ነው ። ተፈጥሮአዊ ሂደቱን ጠብቆ ምግብን መመገብ ብዙ ጥቅም አለው ። መዓዛውን ፣ ጣዕሙን እንድናውቅ ያደርገናል ። ጥርሳችን ጥንካሬ ያገኛል ። ምግብን የሚፈጀው የአካል ክፍልም እየመጣ ላለው የምግብ ዓይነት ዝግጅት ያደርጋል ። ከጠዋት እስከ ማታ ከመቀመጫቸው የማይነሡ የቢሮ ሠራተኞች አሉ ። ሻይ ቡና እዚያው ጠረጴዛቸው ላይ ይመጣላቸዋል ። በየተቋማቱ ሻይ ቡና በእግር ተጉዘው ከሚጠጡበት ቦታ መዘጋጀት አለበት ። አንድ ተቋም የሠራተኞቹን ጤና መጠበቁ ለራሱም ህልውና ወሳኝ ነው ። መንግሥት በከፍተኛ ሁኔታ ሆስፒታሎችን መገንባት ሥራው ነው ። መድኃኒት በውጭ ምንዛሪ ወደ አገር ያስገባል ። ዜጎችም ከአገር ወጥተው በውድ ገንዘብ ይታከማሉ ። በዚህም ውጤቱ አነስተኛ ነው ። የስፖርት ማዘውተሪያዎች በየሰፈሩ ቢገነቡና ጤናማ ማኅበረሰብ መገንባት ቢቻል የአገር ወጪ ይተርፍ ነበር ። ችግርን ከሥሩ መከላከል ውጤታማ ያደርጋል ።

በአገራችን የአንድ ትልቅ ቤተሰብ የልጆች አስተዳደግ የሚያሟላው አራት ነገሮች ነበሩ፡- ትምህርት ፣ ግብረ ገብ ፣ ስፖርትና የዜማ መሣሪያ ማወቅ ናቸው ። ትምህርት ስለ ራሱና ስለሚኖርበት ዓለም ግንዛቤ ይሰጠዋልሰ ። ግብረ ገብ ከራሱና ከሰዎች ጋር የሚኖርበት ትልቁ የመኖሪያ ፈቃድ ነው ። “የሰው አገሩ ምግባሩ” እንዲሉ ። ስፖርት ንቃቱን ፣ ጥንካሬውን የሚጠብቅበት ነው ። የዜማ ዕቃ ፈጣሪውን የሚያመሰግንበት ፣ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚያደርስበት ነው ። ይልቁንም ዕድሜ እየገፋ ሲመጣ ወዳጅ እያነሰ ይመጣልና የዜማ ዕቃ ጓደኛም ነው ። የሰውነት እንቅስቃሴ ከተሟላ አስተዳደግና አኗኗር የሚደመር ነው ። በዚህ ዘመን ስፖርት የሚመለከቱ ብዙ የዓለም ሕዝቦች አሉ ። እንደውም አንድ አባት እንዳሉኝ “ከእግዚአብሔር በላይ ኳስ ተከታይ አለው ።” ኳስ መመልከቱ ያን ያህል ስህተት አይደለም ። ከአምልተ እግዚአብሔር ፣ ከትዳራችን ፣ ከማኅበራዊ ግዳጃችን ከበለጠብን ግን አደገኛ ጣዖት ነው ። “የመጀመሪያውን ስብከት ለእኔ ስጡኝ ፣ የማንቸስተር ጨዋታ አለብኝ” ያለ ሰባኪ እንዳለ ሰምተናል ። እነዚህ የሚያስተምሩት በሥጋ በነፍስ ቢደነቁር አስደናቂ አይደለም ። ቤተ ክርስቲያን የሚቆጭላት አጥታ ቁማር መጫወቻ ከሆነች ቆይታለች ።

ስፖርት ማድነቅና ስፖርት መመልከት ለጤናችን ምንም የሚያደርገው አስተዋጽኦ የለም ። የሚደግፉት ቡድን በመሸነፉ ራሳቸውን ያጠፉ ወጣቶችን በቅርብ ጊዜ ሰምተናል ። የድሀን ቅብጠት የሀብታም አገር በጀት አይችለውም ። ለእውነቱ ካየነው በአገራችን መወራት ያለበት ሰው ስለ መሆን ፣ እንጀራ ስለ መብላት ፣ ስለ ንጽሕናን አጠባበቅ ነው ። የሚገርመው ስፖርት አድናቂዎች ጠጪዎች ናቸው ። የሰውነት ቅርጻቸው የተበላሸ ነው ። የሚደግፉት ቡድን ካሸነፈ በደስታ ይጠጣሉ ፣ ካላሸነፈ በንዴት ይጠጣሉ ። የስፖርት ደጋፊዎች ግብ መጠጥ መጠጣትና ለመጠጡ ምክንያት ማበጀት ነው ። የምናደንቃቸው ስፖርተኞች በብዙ ሚሊየን ዶላር የሚከፈላቸው ሲሆኑ ለእነርሱ ሥራቸው ነው ። እነርሱ ኢትዮጵያ የምትባል አገር መኖርዋን እንኳ አያውቁም ።

ስፖርት የምንሠራው ለተስተካከለ ቅርጽ ቢሆንም ፣ ቅርጻችንን ስናሳይ ለመዋል ግን አይደለም ። ይህ ራስን ማምለክ በመሆኑ በበሽታና በውድቀት ሳይቀጣ አይቀርም ። እዩኝ እዩኝ ያለ ገላ ደብቁኝ ደብቁኝ ይላል ይባላል ፤ ደግሞም እውነት ነው ። ይህ ሕግ ነው ፣ የገዛ አካላችንም ጣኦት ሆኖብን ላስመልክ ካልን በቍስል ይመታል ። ዛሬ ቅርጻቸውን አሳምረው ሀብታም ሴት የሚጠብቁ ድኩማን ወንዶች እያመረትን ነው ። ኤልያብ ተቀምጦ ዳዊት ለንግሥና የተመረጠው ቁመና መስፈርት ስለማይሆን ነው ። ቁመና እያዩ ሹመትና ማዕረግ የሚሰጡ አባቶች አሉ ። ይህ አዲስ አይደለም ነቢዩ ሳሙኤልም የተታለለበት ነው ። “እግዚአብሔር ግን ሳሙኤልን፦ ፊቱን የቁመቱንም ዘለግታ አትይ ሰው እንዲያይ እግዚአብሔር አያይምና ናቅሁት ሰው ፊትን ያያል፥ እግዚአብሔር ግን ልብን ያያል አለው።” (1ሳሙ. 16 ፡ 7) ። ቁመናን እያያችሁ ባል የምታስሱ እኅቶች ከተሰናዱ ሌቦች ራሳችሁን መጠበቅ አለባችሁ ። ሰው ስፖርት የሚሠራው ለራሱ ነው ። ስለዚህ እዩልኝ እያሉ ቪዲዮ መልቀቅ ምን የሚሉት ነገር ነው ? መጽሐፍ እያነበበ ቪድዮ የሚለቅ የለም ። የመጀመሪያው መጽሐፍን እንደ እርግጠኛ ጠላታችን ነው የምናየው ። ሁለተኛው መጽሐፍ የሚያነብ ሰው እዩልኝ ስሙልኝ የሚል ኑሮ የለውም ። ራስን የመሸጥ ግርግር ውስጥ ያለው ይህ ዘመን በድሀ ሕዝብ ፊት ቍርሳቸውን እየበሉ የሚለቅቁ ፣ መኖር ባቃተው ወገን ፊት እየተገላበጡ ከየጂሙ ፎቶ የሚሰድዱ ጨካኞችን ያፈራ ነው ።

አንተ ግን የሰውነት እንቅስቃሴ አድርግ ። ግድ ጂም መግባት አያስፈልግህም ፣ የራስህ ሰውነት የስፖርት መሥሪያም ነው ። ታክሲ ለመጠበቅ አንድ ሰዓት ከመቆም አንድ ሰዓት ተራምደህ እቤትህ ግባ ። በየጂሙ ያለው ወሬና የነጋዴዎች ትውውቅ ፣ ለመቼ ቀን እንደሆነ ባይታወቅም የሰቡ ጎረምሶች የሚታዩበት ነው ። ሌላው ይሥራልኝ ብለህ የተውከው ተግባርህ በራሱ ስፖርት ነው ። ከተፈጠርንበት ሥሪት እየራቅን ስለሆነ ታላቅ የጤናና የሥነ ልቡና ጉዳት ውስጥ ገብተናል ። አንተ ግን በየቀኑ ቢያንስ ለአንድ ሰዓት ያህል የእግር ጉዞ አድርግ ። ከመኝታህ ከመነሣትህ በፊትና በተነሣህ ጊዜ መንጠራራት ፣ ሰውነትህን ማፍታታት አትርሳ ። የትንፋሽ ስፖርት ብቻ ሳይሆን የጥንካሬ ስፖርቶችንም ልመድ ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሰኔ 17 ቀን 2016 ዓ.ም.
2024/06/24 22:38:36
Back to Top
HTML Embed Code: