Telegram Group Search
ንባቡ ተጀምሯል !
ውድ ወዳጆች !

የትውልዳችንን ውጥረት ታሳቢ በማድረግ በሳምንት አንድ ቀን የስልክ የማማከር አገልግሎት ለመጀመር እናስባለን ! ምን ይመስላችኋል ?
እግዚአብሔር ይናገራል 6

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
እግዚአብሔር ይናገራል 6

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
አንተ እኮ !!!

ከለምለም ቅጠል በላይ ደስታዬ ፣
ከሚፈልቀው ይልቅ እርካታዬ ፣
ከመንገድ በላይ መድረሻዬ ፣
የዕለት የዘለቄታ ሳይሆን የዘላለም ማረፊያዬ ፣
በመቃብሬ ላይ ይነሣል ብላህ የጻፍህ ፣
የተጠላሁትን ያፈቀርህ፣ የሰይጣን መልክ ሲሰጡኝ መሳይ ልጄ ያልከኝ ፣ የተነቀፍሁትን ያመንከኝ፣ ወርቅህን እኔ ጭቃው ላይ የጣልህ ፣ መክሊትህን ለአባካኙ የሰጠህ ፣ ጸጋህን ለተራቆተው የናኘህ ...

አንተ እኮ እግዚአብሔር ... ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 1/2016 ዓ.ም.
አሳስብ

(የወጣት አገልጋይ ፈተና)

በግን አንድ ጊዜ ብቻ የሚመልስ እረኛ የለም ። አገልጋይም ደጋግሞ ምእመናንን ከጥፋት መንገድ መመለስ ይገባዋል ። ለመጨረሻ ጊዜ ስህተት የፈጸመ ሰው በዓለም ላይ የለም ። የሰው ልጅ በመውደቅ ሰውነቱን ፣ በመነሣት መንፈሳዊነቱን ይገልጣል ። የአንድ ጊዜ ዕድል መስጠት አማኝን ላያበዛ ይችላል ። ወጣት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ በትዕግሥት እውነትን ማስተማር ፣ ደጋግሞ በመጮህም ምእመናንን ከገደል መመለስ ያስፈልገዋል ። የሚማር ሰው ሁሉ በየትኛውም ዕድሜ ቢመጣ ልጅነት ይታይበታል ። ትምህርት ልጅ ያደርጋልና ። አገልጋዩ ግን የቤቱን ጉድለት ትቶ ፣ የራሱን መጎዳት ረስቶ ቢያገለግልም አሁንም መታገሥ ያስፈልገዋል ። እውነተኛ አገልግሎት ያልተቀበሉትን መስጠት ነው ። ፍቅርን ከሰዎች አላገኘ እንደሆነ ፍቅርን መስጠት ፣ ማንም በውድቀቱ አላዘነለት እንደሆነ ለወደቁት ማዘን የአገልጋይ ወጉ ነው ። የአገልግሎት ፍጻሜው ሰማይ ነው ። ከሰማይ የመጣውን አደራ በሰማይ ያስረክባል ። አገልግሎት አልተመቸም ፣ ሰሚም አልተገኘም ተብሎ የሚቆም አይደለም ። እንደ ነቢዩ ኢሳይያስ ሰው ባይሰማ “ሰማያት ስሙ ፣ ምድርም አድምጪ” ተብሎ የሚጮሁበት ነው (ኢሳ. 1 ፡ 2) ።

ወጣቱ አገልጋይ ማሳሰብ አለበት ። በዕድሜ የገፉ በትክክል መያዛችንን እስኪያረጋግጡ ይደጋግማሉ ። ወጣቱ ግን ይሰለቻል ። በመደጋገም ውስጥ መስማት አለ ። ሰዎች በተለያየ ነገር ልባቸው ይሰረቃል ። እውነቱን እውነት ብለው ለመቀበል ይዘገያሉ ። ያልተቀጡ ኀጥአንን ፣ በመከራ የሚያልፉ ጻድቃንን በማየት “መታዘዝ ምን ጥቅም አለው ” ይላሉ ። ቃሉን ከራሳቸው ፣ በዙሪያቸው ካለው ዓለም ጋር በመታገል ይሰማሉ ። ሰይጣን ቃሉን እንዳንሰማ በመጀመሪያ ፣ እንዳንታዘዝ በመቀጠል ፣ በመጨረሻም ልበ ደንዳና እንድንሆን ይዋጋል ። ማሳሰቢያ የሚል ቃል ያስደነግጣል ። ማሳሰቢያ ቀጥሎ ውጤት ላለው ነገር የሚታወጅ ነው ። እግዚአብሔርን ማሞኘት የሚችል የሚመስለው ሰው አለ ። እርሱ የወደደውን አምላኩ የሚወድለት አድርጎ የሚገምትም አያሌ ነው ። ሲደጋግመው ስህተት ትክክል የመሰለው አለ ። ስላልተቀጣ እግዚአብሔር የፈቀደለት የሚመስለውም አይታጣም ። በነፍሱ እልህ ገብቶ በኃጢአት ጭቃ የሚቦካ አለ ። አንድ ቀን እመለሳለሁ ብሎ ኃጢአት እስከ አንገቱ ደርሶም የሚቀልድ አለ ። ማሳሰብ ግን ያነቃል ። ማሳሰብ በጋራ የማሰብ ውጤት ነው ። አስቤበታለሁ አስብበት ማለት ነው ። አንድን ጥፋት ከሁለት ወገን ማየት እርሱ ማሳሰቢያ ይባላል ። ለዚያ ሰው ማሰብ የሚጠቅመው ሰውዬው ለራሱ ሲያስብ ብቻ ነው ። ሰውን በግድ የሚያድን ፣ በግድም የሚያስኰንን ኃይል በሰማይም በምድርም የለም ።

ተረቶችና የሰው ልጅ ምናባዊ ፈጠራዎች የሚያስደስት ትርኢት አላቸው ። ነገር ግን መጨረሻ የላቸውምና ተስፋ አይሰጡም ፣ ልብን አያሳርፉም ። የክርስትና ሃይማኖት የመጽሐፍ ሃይማኖት ነው ። ሳይንሳዊ ማረጋገጫና ሰዋዊ መላዎች ድጋፍ አይሆኑትም ። ሁሉን ስለደገፈው ጌታ የምንማርበት ነው ። ክፉ ትምህርቶች በዓለም ላይ ተዘርተዋል ። እነዚህ የማይታዩ ማሰሪያዎች ናቸው ። ወጣሁ ሲሉ እንደ አረንቋ ብዙዎችን የሚይዙ ናቸው ። የክፉ ትምህርት አባቱ ሰይጣን ዲያብሎስ ነው ። ትክክለኛ ያልሆነ አስተሳሰብ የተበላሸ ኑሮን ይፈጥራል ። ወጣቱ አገልጋይ እንደ ሎጥ ሚስትና ልጆቹንም ሳይቀር እየሄደ ማሳሰብ እንጂ ቆሞ መጥራት አይገባውም ። የቆሙ ሰዎች ሌላውን ለማቆም ብቁ ናቸው ። እንቅፋት የሚባለው ቆሞ የቀረ ፣ ወይም ወድቆ የቀረ ፣ የራሱ ባልሆነ መንገድ ላይ የተገኘ ነው ። ቆመን ስንቀር ፣ ወድቀን ስንቀር ፣ የራሳችን ባልሆነ መንገድ ላይ ስንገኝ እንቅፋት እንሆናለን ።

ይመስለኛል ፣ ሊሆን ይችላል ፣ እንደ እኔ አተያይ ፣ እገሌ እንደሚያምነው ተብሎ ሃይማኖት አይሰበክም ። ሃይማኖት እርግጥና በራሱ በሚታመነው በክርስቶስ የተሰበከ ነው ። ያለ ዲሲፕሊን ክርስትናን ማካሄድ ፣ አገልግሎትን ባለ አክሊል ማድረግ አይቻልም ። የአመጋገብ ፣ የሰውነት እንቅስቃሴ ፣ የሰው ለሰው ግንኙነት ፣ የሥራ ፣ የአስተዳደር ዲሲፕሊን ያስፈልጋል ። አገልጋዩ ረጅም ርቀት ለመጓዝም ከሰዎች ጋር ያለውን ግንኙነት በልክ ሊያደርገው ያስፈልጋል ። በቂ ስፖርት የሚሠሩ ተራራውን ለመውጣት ይችላሉ ። አብነት የሚያደርጓቸው ሰዎችም አሉ ። እግዚአብሐርን መምሰል ግን ከደብረ ጽዮን ፣ ከማይፈርሰው ከተማ ያደርሳል ። የሁለት ዓለም ወራሽ የሆነውን ሰው ማገልገል መታደል ነው ። ከኋላው ጥሎት የሚሄደው ሥራ ፣ ከፊት የሚቀበለው እምነት እንዲኖረው አበክሮ ማስተማር የወጣቱ አገልጋይ ድርሻ ነው ። እምነት ብቻ በቂ ነው የሚሉ ሰነፎችን ፣ በምግባሬ እድናለሁ የሚሉ ትዕቢተኞችን መገሠጽ አለበት ። በሥጋና በነፍስ ተዋሕዶ የቆመ ሰው ፣ በእምነትና ምግባር ተዋሕዶም የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል ። ማጥፋት እየቻለ የታገሠውን አምላክ እያሰበ ስድብን በደስታ መቀበል እግዚአብሔርን መምሰል ነው ።

የሮማ ጎዳናዎች እንደ ጥንቱ ድምቀት አልታየባቸውም ። ሮም በብዙ ንጹሐን ደም የተጠመቀች የግፍ ከተማ ናት ። ዓለም ሁሉ ሮም እንድትሠራ አዋጥቷል ። የጳውሎስን ቤት ለማግኘት ስዳክር እኔ ጢሞቴዎስ በልቤ ወጣቱን አገልጋይ እንዲህ ስል መከርኩት፡-

“ወዲያው ልታደርገው ያለህን ፈጥነህ አድርግ ፣ ጊዜ የሚሰጠውን ቀጠሮ አብጅለት ፣ ልታደርገው የማይገባህም ለዘላለም አታድርገው ። ቆርጦ መነሣትህ እንጂ ሺህ ጊዜ ማሰብህ ድል አድራጊ አያሰኝህም ። የፈጸምከው ካለ ሌሎች የጀመሩት ነውና ክብር ስጣቸው ፣ የጀመርከው ካለ ሌሎች የሚፈጽሙት ነውና ተተኪዎችን አፍራ ። የዘለቁ ራእዮች ፍቅር ፣ ትሕትናና መንፈሳዊ ቆራጥነት ያለባቸው ስለሆኑ እነዚህን አጥብቀህ ያዝ ። ያጣኸው የሚገኘው የያዝከውን በትክክል ስታየው ነው ። ተፈጥሮ ሁሉ አንተ ብቸኝነት እንዳይሰማህ የከበበህ ቤተ ዘመድህ ነው ። ከሁሉ በላይ የሚራዱህ ቅዱሳን መላእክት አሉና የሚዋጉህን አጋንንት አትፍራ ። የሚያበረታ ጸጋ ፣ የሚያረጋጋ ሰላም ካንተ ጋር ይሁን ! አሜን!

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 19
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 2 ቀን 2016 ዓ.ም.
ወዴት ነህ ?

ወዴት ነህ ? ብለህ አዳምን የፈለግህ ፣ ያለበትን እያወቅህ ያለበትን ያሳወቅህ ፣ በቃል ብቻ ሳይሆን በለቢሰ ሥጋ ወዴት ነህ ? ብለህ የፈለግህ ፣ ከገነት ጫካ እስከ ቀራንዮ የጠፋውን ያሰስህ እኛም በተራችን እንጠይቅህ ወዴት ነህ ?

ለመቆምም ለመሄድም ስንፈራ ፣ ለመግጠምም ለመለያየትም ስንሰጋ ፣ ለመጀመርም ለመጨረስም ስንንቀጠቀጥ ፣ መንፈስህ የራቀን ይመስለናል ። እባክህ ወዴት ነህ ? ገጻችን ሲጠቁር ፣ የልጅ አዋቂው ፊት ትካዜ ሲይዘው ፣ የመኖር መላ ጠፍቶ ሞት እንደ መፍትሔ ሲፈለግ ፣ ድሀ ያለችውን ሲነጠቅ ፣ የፈሩት እየደረሰ ፣ የጠሉት ሲወርስ ምነው አንድዬ ጨከነብን ይሉሃል ። እባክህ ራስህን ግለጥ ፤ ወዴት ነህ ? ሳትለየን የተለየኸን ፣ አጠገባችን እያለህ የራቅኸን መስሎ ሲሰማን ወዴት ነህ ? ብለን በተራችን እንጠይቅሃለን ።

መልሱ ጥያቄ ከሆነብን ጥያቄው ምን ሊመስል ነው ? ሽማግሌው በሰላም ማረፍ ፣ ሬሳው አፈር መልበስ ፣ የወጣው መግባት ፣ የተማረው ማምረት ፣ የሠራው ማግኘት ሲሳነው ወዴት ነህ? እንልሃለን ፣ ለመብላት ይከፍለው የሌለው በሰው እጅ ታግቶ ለመኖር ሲከፍል ፣ ፈጥሮ ላልፈጠረ ተወን እንዳትባል እባክህ ወዴት ነህ ? ዓለም ሰላም ሆኖ እኛ ብቻ የታወክን መስሎ ይሰማናልና እባክህ እንፈልግህ ወዴት ነህ ?

የክፋት አማካሪዎች ምድሩን ሞልተውታል ። ገላጋይ ጠፍቶ ቤተሰብ ያልቃል ። አሸናፊ በሌለበት ወንድማማች ይቀላላል ። ከሚደነቅ ወደሚያደቅ ምዕራፍ ስንሸጋገር ፣ ቀኛችን ግራ ሁኖ ግራ ሲያጋባን ወዴት ነህ ? እንልሃለን ። የጠፋውን አዳም ፈልገህ ያገኘኸው ፣ የጠፋብንን እውነት ፈልገን እስክናገኘው እርዳን ። እየጸለይን ካለመሰማት ፣ ስምህን እየጠራን ከመለያየት እባክህ አድነን ። አሁንም በቀረችው ትንሽዋ አቅማችን ወዴት ነህ ? እንልሃለን ። ስለ ድሆች እንባ አለሁ በለን ።

ሐምሌ 2 ቀን 2016 ዓ.ም.
ማስገንዘቢያ

ቤርያ መጻሕፍት መደብር በአርበኞች ሕንፃ ላይ የነበረውን ሥራ አቁሟል :: ቀጣዩን አድራሻ እስክናሳውቅ መጽሐፍ የምትፈልጉ በቀጣዩ ስልክ ተጠቀሙ

0910531997

ከአክብሮት ጋር !
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (38)

22. ልጆችን በሥርዓት አሳድግ

ምናልባት እኔ ልጅ የለኝም ይህ ምክር እኔን አይመለከተኝም እያልህ ይሆናል ። ልጆች ከእግዚአብሔር የምንቀበላቸው እንጂ የምንቀማቸው አይደሉም ። ሴት ልጅም የልጅ መንገድ እንጂ የልጅ ፈጣሪ አይደለችም ። መውለድ ጸጋ እንደሆነ አለመውለድም ስጦታ ነው ። አብርሃምና ሣራ እስከ መቶ ዓመት ልጅ አልወለዱም ። እግዚአብሔርን በአንድ ልብ ሁነው ለዘጠናና ለመቶ ዓመት ካገለገሉ በኋላ እግዚአብሔር ልጅ ሰጣቸው ። ልጅ የተቀበሉበት ዓላማም የመሢሑን መምጫ መንገድ ለማሳለጥ ነው ። በሌላ አነጋገር ልጅን ለክርስቶስ ወለዱ ። ለጧሪ ለቀባሪ ሳይሆን ልጅን ለሃይማኖት ወለዱ ። እኛ በልጆቻችን ላይ ካለን ዕቅድ እግዚአብሔር በልጆቻችን ላይ ያለው ዓላማ ይበልጣልና ። ነቢይት ሃና ብዙ ዘመን ልጅ በማጣት አልቅሳለች ። በእግዚአብሔር ቤት ባሉ ምእመናን መሳለቂያ እስክትሆን ድረስ ተሸማቃለች ። እግዚአብሔር ልጅ የሚሰጠን ልጅ ያልወለዱትን እንድናሳቅቅበት አይደለም ፤ ልጅ ችሎታ ሳይሆን ስጦታ ነው ። እመ ሳሙኤል ሃና ለራስዋ ልጅን ስትመኝ ዘገየባት ፤ የዘገየው ልጅ ሲመጣ ግን ለእስራኤል ሕዝብ ትልቅ መልስ የሆነው ሳሙኤል ሆነ ። ዘካርያስና ኤልሳቤጥ የወለዱትን ልጅ አላሳደጉትም ። በበረሃ ያደገው ዮሐንስ መጥምቅ ከመሸ የመጣ ነው ። የእነርሱ ደስታ የእግዚአብሔርን ክንድ ማየትና ነቀፌታቸው ሲወገድ መመልከት ነው ። ያልወለዱ የተመሰገኑበትና ብፁዓን የሚባሉበት ዘመን እንዳለ በማሰብ በመውለድ ብቻ መደሰት እንደሌለ እናስተውል ።

አዎ ልጅ ባትወልድም የምታየው ልጅ በሙሉ ያንተ ነው ። ብዙ ደናግልና መነኮሳት የብዙዎች አባትና እናት ናቸው ። እማሆይ ትሬሣን ታውቃቸዋለህ ። የሚሊየኖች እናት የሆኑ መነኵሲት ናቸው ። ልጅነት ብዙ እንደሆነ ፣ ወላጅነትም ብዙ ነው ። ይህ ዘመን የወለዱ ካልወለዱት በላይ የሚጨነቁበት ነው ። በአጭር ቃል ዘመኑ ልጅ ነጣቂ ነው ። ልጅ የወላጆቹን አሳብ ከሚያንጸባርቀው ይልቅ የዘመኑን አሳብ ማንጸባረቅ ይቀለዋል ። አውቃለሁ ባይነት ስለ ነገሠና በዕድሜ የገፉ የሚናቁበት ባሕል ስለ ተመሠረተ ወላጆች በልጆቻቸው ተከድተዋል ። ወላጅ ልጁን መገሠጽና መቅጣት የማይችልበት የሚያለያይ ዘመን ላይ ደርሰናል ። አዎ ልጆች ተሸማቀው ፣ እንዳይጠይቁ ተደርገው በፍርሃት ማደግ የለባቸውም ። በመኖር ፣ በማፍቀርም ከቀደሙአቸው ወላጆች ግን መማር አለባቸው ። ልጆች ቀለብ ከቤት ፣ ምክር ከደጅ ካደረጉ ቆይተዋል ። ወላጆቻቸውን አንሰማችሁም ተስፋ ቍረጡ እያሉ ነው ። አንዳንድ ጊዜ እኛም በወላጆቻችን ላይ የፈጸምነውን ዓመፃ በልጆች ልንቀበል እንችላለን ። ሌላ ጊዜም ልጅ እንደ ራሱ እንጂ እንደ እኛ አይደለም ። ነጻ ፈቃድ አለውና በራሱ መንገድ ቢሄድ የበደለኝነት ስሜት ሊያሰቃየን አይገባም ። የነቢዩ ፣ የቡሩኩ የዳዊት ልጆች አብዛኛዎቹ ክፉዎች ነበሩ ።

ልጅን ስለቀጣነው ብቻ አይታረምም ፣ ልጅ ከቃል ይልቅ በሕይወታችን የምናስተምረው አዳሪ ተማሪ ነው ። ልጅ ከእኛ ጋር ከሚያሳልፈው ዕድሜ ይልቅ ከሰፊው ዓለም ጋር የሚያሳልፈው ሰዓት ይበልጣል ። ንጹሕና ጉልበት ያለበት ሰዓቱን ቢያንስ ለስምንት ሰዓት በትምህርት ቤት ያሳልፋል ። ቤትን ከማሳመር አገርን ማሳመር ለልጆች ወሳኝ ነው ። አገሩ ከወደቀ ምንም ብንጠነቀቅ ልጆቻችን ገንዘብ አይሆኑንም ። አገርን እየዘረፈ ለልጆቹ የሚቀልብ ብዙ ወላጅ አለ ። በጉቦ ያደጉ ልጆች አእምሮአቸው ጤነኛ አይሆንም ። የሚበሉት ደም እንጂ እንጀራ አይደለምና ። የሰለጠነ አገር ልከን ብናስተምራቸው የሰለጠነ ሱስ ውስጥ ይገባሉ ።

የመጀመሪያ ልጅ የደስታችን መነሻ ነው ። ከዚህ በፊት በልጅ ተደስተን ስለማናውቅ የመጀመሪያው ልጅ ትልቅ ፍስሐ ያመጣልናል ። የመጀመሪያው ልጅ ከልምድ ማነስ የተነሣ በጣም ስለምንጠነቀቅለት ነጻነት የሚያጣ ይሆናል ። እርሱን የሚመስል ልጅ እቤት ውስጥ ስለሌለ ውሎው ከእኛ ጋር በመሆኑ ያለጊዜው ይበስላል ። ፍጹም እንዲሆን ወይም እንደ ትልቅ እንዲያስብ ስንፈልግ ብዙ ዱላ ልናበዛበት እንችላለን ። የመጀመሪያ ልጅ ፈሪ ወይም ቂመኛ መሆኑ የተለመደ ነው ። አሊያም የራሳቸው ጉዳይ ብሎ ቤተሰቡን ችላ የሚል ራስ ወዳድ ይሆናል ። ሌላ ጊዜ ደግሞ እንደ ወላጅ ራሱን ቆጥሮ ቀንበር የሚሸከም ይሆናል ። ሁለተኛው ልጅ ሲመጣ ዓይን ሁሉ ከእርሱ ላይ ይነሣል ። በዚህ ምክንያት በቅንዓት ውስጡ ይጎዳል ። አልበላም እያለ የሚያምፀው የራሱን ጨርሶ የሌላውንም ቢበላ ደስ ይለዋል ። ራሱንም በገዛ ቤቱ ባዕድ ያደርጋል ። አንዳንድ ጊዜ የመጀመሪያ ልጆች ወላጆቻቸውን ክደው አባትና እናቴ አይደሉም እያሉ በደጅ ያወራሉ ። ፍቅር የተነፈጉ ፣ የመጀመሪያውን እንክብካቤ ያጡ ሲመስላቸው የደጅ ኀዘኔታ ለማግኘት በፈጠራ ታሪክ ራሳቸውን ያስተዋውቃሉ ። የሚገርመው የፈጠራ ታሪካቸውን እያመኑት ይመጣሉ ።

የመጀመሪያ ልጅ ላይ ሥራ መሥራት ቀጣዮቹ እንዲባረኩ ያደርጋል ። ቀጣዮቹ ከወላጆቻቸው ይልቅ የበኵሩን ልጅ መከተል ይወዳሉ ። ስለዚህ የመጀመሪያ ልጅን ከመጠን በላይ መንከባከብ ተገቢ አይደለም ። ምክንያቱም አይዘልቅምና ። “የማይዘልቅ ጸሎት ለቅስፈት” እንዲሉ ። ይልቁንም በኵሩ የእግዚአብሔር ነውና ለእግዚአብሔር መስጠት ፣ አገልጋይ ማድረግ ይገባል ። በኵርን ለእግዚአብሔር መስጠት ስንከለክል 12 ወልደን አንዱም የማይወደን እየሆነ መጣ ። ሰንበትን ለእግዚአብሔር ስንከለክል በሰንበት እየሠራንና እየተማርን በረከትና እውቀት የለሽ ሆንን ። እግዚአብሔርን ሰርቆ የበለጸገ ማንም የለም ።


ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 5 ቀን 2016 ዓ.ም.
Audio
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 25
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ማር . 6፣ 1-ፍጻሜ ዳሰሳ
እግዚአብሔር ይናገራል 7

በ#ዲያቆን #አሸናፊ #መኮንን የተዘጋጀ ስብከት

አሁን በቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል ። ይከታተሉ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ትምህርቶችና ስብከቶች ለመከታተል ከሥር የተቀመጡትን ገጾች ይመልከቱ፡-

https://www.tg-me.com/Nolawi ኖላዊ/com.Nolawii

https://www.tg-me.com/nolawisebketoch

https://www.facebook.co m/ashenafi.mekonnen.357

https://youtu.be/3qfQp9yYmHY

www.ashenafimekonen.com
Audio
እግዚአብሔር ይናገራል 7

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ከፍ ካለው በላይ

የመጣው ሄደ፣ የሄደውም አይመጣም። የነገሠው ተሻረ ፣ የተሻረው ዳግም አይቀባም። የተሞገሰው ተረገመ፣ የተወገዘው ስሙ ያው ሆኖ ቀረ ። ባለ ጠጎች ደኸዩ ፣ አለ የሚባል ጠፍቶ ነበር የሚል ቃል በምድር በረከተ። ጎዳናው ይወስዳል ይመልሳል፣ ሕይወት ግን ያንን ጓደኛ፣ ያንን ውብ ዘመን፣ ያንን ክብር፣ ያንን አንቱታ አትመልስም ። በዘመኑ ታላቁ እስክንድር ዓለም ፈራው ፣ ዛሬ ፈሪዎች አይፈሩትም። እግዚአብሔር ማነው ? ያለው ፈርዖን ሰጠመ ፣ እስካሁን ትንሣኤ አላገኘም ። አውሮፓ ዱር ሳለ ግሪክ አሰለጠነች፣ ዛሬ ግሪክ በዕዳ ተዘፍቃ ብዙ ረዳት ሊያቆማት አልቻለም ። የጰጰሱ ተሳሳቱ ሲባል ይወገዛሉ፣ አስኬማና በትረ ሙሴ መልሱ ይባላሉ ።

ቆንጆዎች ቆንጆ ነበርሁ ሲሉ ማን ያምናቸዋል? ያ ውበት ላይመለስ ጥላሸት ተቀብቷል ። ያ ተክለ ቁመና ፣ ያ እንደ ፀሐይ የሚያበራ ገላ ፣ ያ መሬት ለመርገጥ የሚጸየፍ እግር ዛሬ ጭቃ ላይ ተኝቷል ። ቤቱን ለደቂቃ የማያምነው ለዘላለም ጥሎት ሄዷል። የሚሳሳለትን ንብረት ዛሬ የማያውቀው ሰው ይጫወትበታል ። የሕይወት መንገድ መሄጃ እንጂ መመለሻ የለውም ። እኛ ወደ እነርሱ እንጂ እነርሱ ወደ እኛ አይመጡም። የዓለም ከፍታ በዝቅታ ፣ ዙፋን በመቃብር ፣ ዳኝነት በእስረኛነት ይለወጣል ። ያንተን ልዕልና ፣ አማኑኤል ሆይ ያንተን ክብር ካላሰቡ ልብን ያደክማል ።

ከፍታህ ዝቅታ የለውም፡፡ ነበረ ተብሎ ታሪክ አይነገርልህም። ሁልጊዜ ያው ነህ ። እንዳንተ የሸመገለ የለም፤ እንዳንተም አዲስ የለም ። መጀመሪያ ላይ ቆመህ መጨረሻውን ታውቃለህ፤ እያወቅህ ግን ዝም ትላለህ። ለድሀው እንጀራ ትሰጣለህ ፣ መልሶ ሲክድህ የሚያማልድ ሰባኪ ትልክበታለህ ። በልካችን አትከፍለንም ፣ በልክህ ታኖረናለህ ። መሰላል ላይ የወጡ ይወርዳሉ። በአየር ላይ የተንሳፈፉ መሬት ይናፍቃሉ ። ከፍ ካሉት በላይ ከፍ ያልከው አንተ ግን በማይነገር ቅድስና ትኖራለህ ። ለጠባይህ ዝቅታ ፣ ለዙፋንህ መናወጥ የለበትም ። የዛሬው አሸናፊ የሁልጊዜ አሸናፊ አይደለም ። የዛሬው ፈራጅ የሁልጊዜ ፈራጅ አይደለም ። የእኔ አምላክ ግን የማለፍን ሥርዓት ድል ትነሣለህ ። ሳትቀበል ትሰጣለህ ። ሳትሾም ትሾማለህ ። አዎ ከፍ ካሉት በላይ ከፍ ብለሃል ። ልዕልናህን ልዕልናህ ያመሰግናል ። በክረምቱ ዝናብ ነጠብጣብ ልክ ብትመሰገን ልክህ አይደለም ።

በምድር ላይ ያንተ ትልቅ ነገር እኛ ነን ። በሰማይና በምድር የእኛ ትልቅ አንተ ሁንልን ! 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 8 ቀን 2016 ዓ.ም .
የምእመናን ስሞች

በሚል ርእስ አራት ተከታታይ ትምህርቶች በየቀኑ ይለቃቃሉ ! እንድትከታተሉ ይሁን!





ዘመናችሁ ይባረክ!
Audio
የምእመናን ስሞች 1

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
Audio
የምእመናን ስሞች 2

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የሕይወት ሥነ ሥርዓት (39)

23. ከሰዎች ጋር ግንኙነትህን አሳምር

“ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ።” ሮሜ. 12፡18 ። ሐዋርያው “ቢቻላችሁስ” አለ ። ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም መኖር ከባድ ነውና ። ቢቻለን ከሁሉም ነገድ ፣ ከሁሉም ሃይማኖት ጋር በሰላም መኖር ይገባናል ። ምድር የሁሉም እንጂ የአንድ ሃይማኖትና የአንድ ወገን አይደለችምና ። ለሁሉም እንደ ሥራው የሚፈርድ አምላክ አለና ሳንፈራረድ ከሁሉም ጋር በሰላም መኖር መታደል ነው ። በዚህ ምድር ላይ ልከኛ ነዋሪ የሚባለው ከሰዎች ጋር ያለውን ግንኙነት የሚያሳምር ነው ። ከሰዎች ጋር የዝምድና ፣ የሃይማኖት ፣ የጓደኝነት ፣ የሥራ ባልደረባነት ፣ የነጻነት ትግል ፣ የአገር ፍቅር ሊያገናኘን ይችላል ። መቼም ሃይማኖት ላለው ሰው ከዝምድና ሁሉ የሚበልጠው በክርስቶስ ያወቁት ወንድምና እኅት ነው ። ምድራዊ ዝምድና ሁሉ መቃብር ይገታዋል ። በክርስቶስ መዛመድ ግን ከሞትም ባሻገር የሚዘልቅ ነው ። በኖርኩበት ዘመን መንፈሳዊ ዝምድናን የሚያከብር ብዙ አላየሁም ። የሥጋ አባቱን ምሥጢር ደብቆ የሃይማኖት አባቱን እንከን በአደባባይ የሚያወራ ብዙ ነው ። የሥጋ ወንድሙ ቢበድለው ይቅር እያለ የሃይማኖት ወንድሙን ግን ጠልቶ የሚቀር አያሌ ነው ። የእግዚአብሔር ፈቃድ ሰው ከሰው ጋር እንዲኖር ነው ። ከሌላው ጋር ለማበር ሰው መሆን በቂ ነው ። በሽታው ሲመጣ ጥቁርና ነጩን በአንድነት ይፈጀዋል ። በአንድ ዓይነት በሽታ እየታመምን በአንድ ዓይነት ፍቅር መኖር አለመቻል ያሳዝናል ።

ከሰዎች ጋር ያለንን ግንኙነት ለማሳመር ከልብ ሰዎችን መውደድ ቀዳሚው ነው ። ልባዊ ፍቅር ባለበት የመለኮት መገኘት አለ ። በዚህ ዓለም ላይ ብዙ ዓይነት ፍቅሮች አሉ ። እግዚአብሔርን መነሻ ያደረገ የአጋፔ ፍቅር አለ ። ሥጋዊ ስሜትን መነሻ ያደረገ የወንድና የሴት ፍቅር አለ ። ይቅርታን ገንዘብ ያደረገ ጠላትን የምንወድበት ፍቅር አለ ። እኩያነትን ያገናዘበ የጓደኝነት ፍቅር አለ ። ሰዎችን ከልብ ስንወድድ ውስጣችን እውነተኛ እንደ ሆንን ይመሰክርልናል ። ሰዎች በዚህ ዘመን ሲወድዱን እንጠራጠራለን ፣ ሲጠሉን ግን ከልብ እናምናለን ። ፍቅርን መስጠት ብቻ ሳይሆን መቀበል አልቻልንም ። ደግነት እያጠራጠረን ፣ ለምን ቸር ሆኑ እያልን ነው ። መልሰን ደግ ሰው ጠፋ እያልን እናማርራለን ። ስለ ብርቅዬ እንስሳት መጥፋት የሚያለቅሰው ያጠፋቸው ያው የሰው ልጅ ነው ። የገፋነው ደግነት ዛሬ በስእለት የማይገኝ እየሆነ ነው ። ሰውዬው እኔን ከመውደዱ በፊት ቀድሜ መውደድ ታላቅነት ነው ። የእግዚአብሔር ፍቅር መፍሰሻ ይፈልጋል ፣ በእኛ ወደ ሌሎች ለመፍሰስ ይሽቀዳደማል ። ሰዎችን በሁለተኛ ደረጃ በግልጽነት መቅረብ ያስፈልጋል ። በዚህ ዓለም ላይ ተሸፍኖ የሚሰነብት እንጂ ተከድኖ የሚቀር ምንም ነገር የለም ። ግልጽነታችን ግን የእብደት ታናሽ ወንድም እንዳይሆን መጠንቀቅ አለብን ።

ለሰዎች መገኘት አለብን ። ይህ ሦስተኛው የግንኙነት መርህ ነው ። ሰዎች ለእኛ የሚያስፈልጉን ቀን እንዳለ ሁሉ እኛ በምናስፈልጋቸው ቀን ሳይጠሩን መገኘት አለብን ። እግዚአብሔር መከራችንን በተለያየ ቀን ያደረገው አጽናኝ እንዳይታጣ ብሎ ነው ። ሲታመሙ ፣ ሲታሰሩ ፣ እንግድነት ሲመጡ ፣ ኀዘን ላይ ሲቀመጡ አለሁ ማለት አለብን ። በዚህ ዓለም የቅርብ ዘመድ የሥጋው ሳይሆን የቅርብ ጎረቤት ነው ። ኑሮአችን ገለልተኛ መሆን የለበትም ። ማንም እንዳይደርስብኝ ብለን በር ዘግተን መኖር ሕይወትንም ሞትም የሚያበላሽ ነው ። የሰለጠነው ዓለም የፈጠረው የግለኝነት ኑሮ ሰውዬው ሞቶ እንኳ ሬሳው እንዲበላሽ ያደረገ ነው ። መሰልጠን የምንለው ገደብ ከሌለው ለዚህ የሚያደርስ ነው ።

ሁሉን ነገር ክፍት ማድረግ የለብንም ። ይህ ዓለም የልክ ዓለም ነውና ለወዳጆችም ልክ መስጠት አለብን ። ሁሉም ነገር የሚወራው ፣ ሁሉም ነገር ክፍት የሚደረገው ለእግዚአብሔርና ለእግዚአብሔር ሰው ብቻ ነው ። አንዳንድ ጊዜ የትዳር ጓድም የማያውቁትና የማይሸከሙት የሕይወት ምሥጢር ይኖረናል ። ሰዎች ሁሉንም ነገራችንን የማወቅ መብት የላቸውም ። ንስሐና ጸሎት የሰውን ምሥጢራዊ ሕይወት የሚያግዙ ናቸው ። ሄደው እንዲመለሱ መፍቀድ አለብን ። ሰዎች በጣም መልካም ስንሆንላቸው ከዚህ የተሻለ መልካም ሌላ ቦታ አለና ልሂድ ብለው ያስባሉ ። ሄደው እንዲመለሱ መፍቀድ አለብን ። አንዳንድ መልካሞች ግን ከሸኙ በኋላ በሩን ዳግም አይከፍቱምና መጠንቀቅና አክብሮ መያዝ ይገባል ። ሰዎች እንዲሄዱ ካልፈቀድንላቸው ብዙ ነገሮች ይከሰታሉ ። የመጀመሪያው በልቡ የሄደን ሰው በአካል መያዝ በድን ታቅፎ መኖር ነው ። ሁለተኛ እኛ በእግዚአብሔር ብቻ እንደምንኖር ሁሉም ማወቅ አለበት ። እየወደዱን እንጂ እያስፈራሩን መኖር የለባቸውም ። ይህ ልካቸውን አጥተው እንዲፋንኑና እንዲባልጉ ያደርጋል ።

ከሰዎች ጋር ባለን ግንኙነት በእውነት ሲመለሱ በይቅርታ መቀበል ነው ። አንዳንድ ይቅርታዎች በውስጣቸው ክፋት ሊኖራቸው ይችላልና ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል ። ያልጨረሱትን ክፋት ለመጨረስ በይቅርታ ስም የሚመጡ ፣ እኛን አባብተው ጥቅም ፍለጋ እንደ ድመት የሚመለሱ ይኖራሉ ። እውነተኛ ይቅርታዎችን መቀበል ተገቢ ነው ። እግዚአብሔር ከሰው ጋር የሚኖረው ሰውን ይቅር እያለው ነው ።

ግንኙነትን የሚጎዱ ነገሮች አሉ ። የጋራ ፍቅር አለመኖር የግንኙነት ጸር ነው ። በአንድ ሰው ፍቅር የሚቀጥል ወዳጅነት ፣ የሚቆም ቤት ፣ የሚሠራ ተግባር አይኖርም ። የእኔ ፍቅር ብቻውን በቂ ነው በማለት ወደ ትዳር መግባት ለመውጣት ነው ። ጠላትህን ውደድ በሚል ፍቅር ወደ ትዳር ቢገባ ጉዳቱ የከፋ ነው ። አለመከባበር የግንኙነት አፍራሽ ነው ። ሐሜት ግንኙነትን በብርቱ ይጎዳል ። ስለ ወዳጅህ መልካምነት በሌላ ቦታ ፣ ስለ ጉድለቱ ግን ለራሱ ተናገር ። ጥቅመኛነት ወዳጅህን ለጉዳይህ ብቻ መውደድ አንድ ቀን ለዘላለም እንድትለየው ያደርግሃል ። ሞኝም የሚነቃበት ቀን አለ ። ራስ ወዳድነት የግንኙነት ትልቅ ጸር ነው ። ራስን ብቻ ማዳመጥ ፣ የራስን ፍላጎት ብቻ መከተል ሌጣ ሰው ያደርጋል ። ጨካኝነት የግንኙነት ጎጂ ጠባይ ነው ። ወደቀ ብሎ ወዳጅን መርገጥ ፣ ተራቆተ ብሎ ለዓለም ማሳየት ይህ ከባድ ወንጀል ነው ። አላባብሶ ኑሮ የወዳጅነት ጸር ነው ። ተወው ተይው መባባል ግንኙነትን ይጎዳል ። በሁለት ዓይን መተያየት ፣ በሁለት ጆሮ መስማት የግንኙነት ጸር ነው ። አንዱ ዓይን ስህተትን ሲያይ አንዱ መጨፈን አለበት ። ሰዎች አንድ ጊዜ እንኳ እንዲሳሳቱ መፍቀድ አለብን ። የሃያ የሠላሳ ዘመን ጓደኝነትን በዛሬ ክስተት አፈር ማልበስ አንገት የለሽ መሆን ነው ።….

ይህን የግንኙነት አሳብ ብቀጥለው ደስ ባለኝ ነበር ፣ የአገሬ አንባቢ ስልቹ ነው ። የሚጠቅመውን ትቶ የማይጠቅመውን የሚያስስ ነው ።



ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሐምሌ 12 ቀን 2016 ዓ.ም.
Audio
የምእመናን ስሞች 3

# ዲያቆን # አሸናፊ # መኰንን
Audio
የማርቆስ ወንጌል ትርጓሜ 26

ማር.6 ፥ 1- 6

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ውድ ወዳጆች ለዛሬ ቀናችሁ፣ ለዛሬ ምሽታችሁ የማርቆስ ወንጌል ክፍል 26 ን እንድት ሰሙ እጋብዛችኋለሁ !

እኔ የክርስቶስ ባሪያ
2024/07/20 07:46:07
Back to Top
HTML Embed Code: